18304
✔በየቀኑ ምርጥ ምርጥ የጥበብ ስራዎችን ለማግኘት የቻነላችን ተከታይ ስለሆኑ እናመሰግናለን። ✔ @getem @serenity13 ✔ @wegoch @Words19 ✔ @seiloch ✔ @zefenbicha Creator @leul_mekonnen1
ለምን 'ለምን' ሞተች??
(ገብርኤላ ይመር)
First we mourn the grief we bear, and then later we mourn the grief we've caused"
-Meron Hadero, Kind stranger
አንዲት ከሰዓት አንድ የእስራኤል መስፍን ያስጨነቁት ጠላቶቹን ሊገጥም ከመውጣቱ በፊት ጠላቶቹን በእጁ የጣለለት እንደሆን ወደ ቤቱ ሲመለስ ሊቀበለው የወጣ ማንኛውም ነገር ሊሰዋለት ከአምላኩ ጋር ቃል ተገባባ። መስፍኑም ድል አደረጎ ወደ ቤቱ በደስታ ሲመለስ ወንድምም እሀትም ያልተወለደላት አንድያ ሴት ልጁ ልትቀበለው ወጣችና ደስ የተሰኘች ነፍሱን ስለ ገባው ቃል አዉከቸው። እርሷም አለች "አንዴ ከአምላከሀ ጋር ቃል ይዘሃልና እሰዋለሁ ግን ከዚያ በፊት ግን ከእስራኤል ልጆች ጋር ያስቆጥረኛል ላልኩት ለድንግልናዬ ላልቅስለት!"
አሸንዳ: የመስፍኑ ዮፍታሔና የልጁ ታሪክ መጽሐፈ መሣፍንት 11:34) አንደኛው የአሸንዳ በዓል አጀማመርምክንያት ሲሆን የእስራኤል ልጃገረዶች በዓመት አራቴ ስለ ዮፍታሔ ልጅ የማልቀስ ልማድ ነበራቸው። ይህም ባህል ወደ ሀገራችን ከታቦተ ጽዮን መምጣት ጋር ተያይዞ ከገቡ ትውፊቶች አንዱ ሆኖ በየዓመቱ ልጃገረዶች አሸንዳ፣ ሻደይና ሶለል ብለው የሚያዘክሩት በዓል ሆኗል።)
(በ1966 የአዲስአበባ ዩኒቨርht ተማሪዎች የንቅናቄ መሪያቸው የነበረውን የተማሪ ጥላሁን ግዛውን ግድያ ለመቃወም በወጡት የተማሪዎች ሰልፍ የተዜመ: “ጥላሁን ለምን ለምን ሞተ"
ኔግሮ የሚባል ፍሬንድ ነበረኝ ፀባይኛ ነው፣ ሌባ ነው፥ እናቱን ይወዳታል፥ ትምህርት አይገባውም፤ ተንኮል፣ ኳስ ፣ጆተኒ ፣ ትረባ ጎበዝ ነበር።
በአንድ ሴሚስተር መቶ እና ሁለት መቶ መፅሃፍ ይሰርቃል መቼ? ...እንዴት?...ከማን?... አላውቅም!
መጨረሻ ላይ ውጤቱን እየሳቀ ይነግረኛል።
አንድ ቀን እንኳን ሲሰርቅ ተይዞ አያውቅም !
የሰረቀውን መፅሐፍ ሲሸጥ አብሬው ሄጄ አውቃለሁ። ከሚገዙት ጋር ደምበኛ እንደሆነ ሰላምታ አለዋወጣቸው ያስታውቃል። አሻሻጡ የሰረቀ ፣ ሳይለፋበት ያመጣ አይመስልም፤ በቸልታ አይደለም። በርጋታ እንደትልቅ ሰው... "አይሆንም...፣ ይቅር...፣በቃ፣ ጨምር " እያለ ነው ።
እናቱን "ሸቅዬ... እዛ ማዶ ያሉት ሃብታም ሰዎች፤ ለእናትህ ስጣት ብለው ብር ሰጡኝ" እያለ እንደሚሰጣት ነገሮኝ ያውቃል ።
ሰባተኛ ክፍል ፣ ስምንተኛ ክፍል እያለን እናቱን ያግዛት ነበር ። ይወዳታል፤ አወዳደዱ እንደትልቅ ሰው ነው። "ማሚዋ ደብሯታል ...አሟታል. . . ገበያ ቀዝቅዞባታል" እያለ ያስብላታል።
ከጓደኛው አይሰርቅም። ለጓደኛው ለኔ ለሚለው ሰው ይሳሳል።
አይኖቹ ትናንሽ ናቸው፣ አካባቢውን በትኩረት ያያል፣ ከወሬ ሁኔታን ያያል። ሌባ መሆኑን ብዙ የሩቅ ሰዎች አያውቁም።
ኔግሮ ቁርንጫጭ ፀጉር ያለው፣ ድቅቅ ያለ ገላ ያለው፣ ሲስቅ ቀጭን ድምፅ የሚያወጣ ልጅ ነበር ።
አንዳንድ ቀን ይፎርፍና ሜዳ ጥግ ውኃ ልኩ ጋር ብቻውን ይሆናል ። ዝም ይላል ኳስ አይጫወትም። ቀጭን ድምፅ እያወጣ የሚስቃት ሳቅ አትኖርም። ለመኮረጅ ብዙ አይሰቃይም።
...ጨዋታ ያበዛል...።
ስለ አባቱ አላውቅም፤ እናቱ ግን ትምህርት ቤታችን በር ጎን ላይ ቃርያ ፣ ቲማቲም፣ ነጭ ሽንኩርት፣ ድምብላል፣ ኮሰረት፣ ስኳር ድንች ...ምናምን ይሸጣሉ። ብዙ ደንበኛ ያላቸው አይመስለኝም። ስንወጣ ስንገባ የደራ ገበያ አንድም ቀን አይቼ አላውቅም ።
ኔግሮ የትምርት ቤት ስሙ መቆያ ነው። እኛ ነን ኔግሮ የምንለው።
እኛ ትምህርት ቤት የሚማሩ የሰፈሩ ልጆች ሲጠሩት ሰምተን መሰለኝ መቆያን ትተን ኔግሮ የምንለው።
መቆያ የሚባለው ክላስ ስም ሲጠራ ብቻ ነው። ኔግሮ ሲባል ነው እሱም ደስ የሚለው።
የሆነ ቀን ሃይሚ ግርማ መፅሃፍ ጠፍቶብኝ ኔግሮ ሰጠኝ አለችኝ። ጠየኩት "ከራሷ ቦክመህ ለራሷ ገጫሃት ኣ?" ስለው ፤ ሲስቅ የሚያወጣትን ቀጭን ድምፅ አውጥቶ ሳቀ "ባክህ እኔ እንደኔ ችስታ እናት ካለው ቤተሰብ አልሰርቅም "አለ ።
ከስምንት ወደ ዘጠኝ ስንዘዋወር ኔግሮ ታስሯል አሉን። ስሰማ "ዕድሜው ለእስር ደርሷል ወይ?" ብዬ ያኔ አልጠየኩም።
የመንግስት ትምህርት ቤት ስለተማርን ለብዙ ነገር ከዕድሜያችን በላይ ነበርን። የሚታሰሩት በግሩፕ የሚጣሉ ልጆች ስለነበሩ ብዙ አልገረመኝም።
መስከረም አስራ ሰባት ቀን ኔግሮ ሞተ አሉን። እናቱን ስናያቸው ጥቁር ለብሰዋል፥ ጉስቁልናው ብሶባቸዋል። ጉሊት የደረደሩት ከዚህ ቀደም ለመሸጥ ከሚደረድሩት በዐይነትም በመጠንም ቀንሶ አየሁ ።
ሞትን ያኔ ነበር በቅርብ ያወኩት ....በቅርብ የማውቀው፣ ሲያወራ የሰማሁት፣ አብሬው የተጫወትኩት ጓደኛዬ ሞተ ሲባል። ያኔ ነው ለመጀመሪያ ግዜ ያመንኩት።
የታሰሩበት ክፍል የነበረው ካቦ መቶት ነው ይላሉ፤ አንዴ ፖሊስ መቶት ነው ይላሉ፤ አንዴ ታሞ ነው ይላሉ ....
ኔግሮ ሞተ። እውነት ነበር!
"ልጅ ይሞታል እንዴ?!" አልኩኝ
ለምን መቆያ አሉት ግን እናቱ??
በዛ ዕድሜው እንዴት በዛ ልክ አሰበላቸው??
በምን ይሆን የሚፅናኑት??
ለምን ሌባ ሆኖ ለጓደኞቹ ታመነ??
እንዴት የሰረቀውን እንደትልቅ ሰው አስቦ ተከራክሮ ሸጠ?? ላለፋበት ነገር እንዴት ዋጋ ሰጠ?? ለምን ምንም ከሌላቸው ሰዎች አልሰርቅም አለ??
በዛ ዕድሜው እንዴት አረጀ ?
እሺ ይሁን መርህ እና ሌብነት እንዴት አብሮ ሄደለት!!
እኔንጃ ኔግሮ ግን ሞተ አሉ !!!
By Adhanom Mitiku
@wegoch
@wegoch
@paappii
ስማቸውን ጥለው የሚሄዱ ኤክሶች!
(አሌክስ አብርሃም)
ኪያ ደወለችና " ገሲ አይንሽን አላይም ከዚህ በኋላ ብሎኝ ሄደ" ብላ አለቀሰች። ገሲ ገጣሚ ወዳጀ ገሰሰ ነው። በፍቅር አንድ አመት ቆይተው ነበር።
"እንዴ ለምን ?"
"እኔጃ በቃ አያምነኝም ፣ የሰው ወሬ እየሰማ ይበሳጫል!" ማልቀሷን ቀጠለች።
"ለዛ ነው ሰሞኑን የተለየሁሽ ለት ...ሴት ሞልቷል ባገሩ ፣ ቃልሽን የበላሽ... የጉም ጅብ ፣ የፀሐይ ቀበሮ የሚል ግጥም አከታትሎ ሲለጥፍ የነበረው? አልኩና ሁለቱንም ለማስታረቅ ቀጠርኳቸው። ልክ እንደገብረመድህን ፍልጥ ይዤ መሄድ ነበር የቀረኝ። ትዝ ይለኛል ቦታው ሁሉ ብሔራዊ የነበረች ኮፊ ሾፕ ፎቅ ላይ።
"ምን አጣላችሁ ደግሞ ?" አልኩ
ገጣሚ ወዳጀ ስካርቩን አስተካከለና "ተወኝማ አብርሽ! ሁልጊዜ የምትጠራኝ በሌላ ወንድ ስም ነው...ዳኒ ትለኛለች፣ ሳሚ ትለኛለች፣ ኬ ትለኛለች ኤም ትለኛለች አሹ ትለኛለች መረረኝ አልበዛም? ምንድነው ይሄ ሁሉ ወንድ ? ምንድነው? አፏ ላይ እኔ የለሁም።" አለ በብስጭት።
"አፍ ላይ ምን ታደርጋለህ? አንተኮ ልቧ ውስጥ ነህ ገሴ!" ብየ ወደደረቷ ስጠቁም ትልልቅ ጡቶቿን አይቶ ትንሽ ተረጋጋ። ወዲያው ጣልቃ ገባችና በችኮላ እጇን እጁ ላይ ጣል አድርጋ እንባ የሞሉ አይኖቿን አይኖቹ ላይ እያንከባለለች በሚያሳዝን ድምፅ ....
"አልተረዳኸኝምኮ ግርምሽ... " ከማለቷ አበደ፣ ስካርቩን ጣለ!
"ግርምሽ ደግሞ ማነው? ያለዛሬም አልሰማሁት። ማነው....?"
@getem
@getem
@paappii
'የማያረጅ ውበት የማያልቅ ቁንጅና'
ከ10 አመታት በፊት (እንደኛው አቆጣጠር በ2007 ዓ.ም.መሆኑ ነው) እሁድ እሁድ በኢ.ቲ.ቪ የሚተላለፍ "መለከት" የተሰኘ ተከታታይ ድራማ ነበረ።ያንኑ ድራማ ከሰሞኑ መገረብ ጀመርኩና አንድ ነገር ታዘብኩ...እንደ ሀገር ሊያሳስበን የሚገባ ትልቅ ጥያቄም ተፈጠረብኝ።"አለማየሁ ታደሰ መቼ ነው የሚያረጀው?"
ሴት አያቶቻችን 80 አልፏቸውም እንጀራ ጋግረው ይበላሉ።ወንዶቹ እርሻቸውን ለልጆቻቸው 'እንደፍቃዳችሁ አድርጉት' ብለው አይተውትም።እኛ በ20 አመታችን የሚያቅተንን እነሱ በ80 አመታቸው ሲያቀላጥፉት አይተን ''እንዴት?" ስንል "እነሱ እንደናንተ ምናምንቴ አይበሉም...በማርና በቅቤ ነው ያደጉት" ይሉናል።እና አለማየሁ ታደሰ የጢንዚዛ ማር ነው የበላው?አባቴ እንደነገረኝ አለማየሁ የገነት ንጋቱ የቴአትር መምህር ነበር።ጥንት "ዴዝዴሞና" የሚል ፊልም ላይ ሳየው ጀምሮ አሁን በስንቱና አጋፋሪ ላይ ሳይቀር መልኩ አንድ ነው።የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ኢትዮጵያን አዳርሶ ኤርትራና ሶማልያ ቅርንጫፍ ለመክፈት ዝግጅቱን ጨርሶም አለማየሁ አንዲት ነጭ ፀጉር አላወጣም።ካስቀመጥኳቸው መላምቶች አንዱ 'vampire ሊሆን ይችላል' የሚል ቢሆንም የጥርሶቹን አደራደር ሳይ ሀሳቤን ተውኩት።የሆነው ሆኖ አለማየሁ ስስታም ነው።እኒያ ወጣቶቹ የጥበብ ሰዎች በየቃለ መጠይቁ እድሜአቸውን ሲጠየቁ ከሚተናነቃቸው ምናል ምስጢሩን ሹክ ቢላቸው?ለኔስ ቢተርፍ ምናለበት?የአለማየሁ ሰውነት የሰናፍጭ ቅንጣት ታህል እንኳን የእድሜ ነፋስ ሽው ሳይልበት እኔ "ሚጡ" ከመባል አልፌ የነሚጡ እናት የመሆኛ ዘመኔ ጥሎኝ ኮበለለ...የእናቴ የጠጉር ሽበት አንድ አንድ እያለ መላውን ጭንቅላቷን አዳረሰው...አባቴ ደርግ በሸለመው ከዘራ ይሰራ የነበረውን ሮንድነት ትቶ ጡረታ ከወጣ ዘመን የለውም...አለማየሁን ስናውቀው ያልተወለደው ታናሽ ወንድሜ ቁመት በልጦኝ በመሀላችን ያለውን የ10 አመት የእድሜ ኬላ ጥሶ "ከጎረምሳ ጋር አየሁሽ"በሚል ተልካሻ ምክንያት በኩርኩም እየነረተኝ ነው።እና...አለማየሁ መቼ ነው የሚያረጀው?
By ዘማርቆስ (@wogegnit)
@wegoch
@wegoch
@paappii
#SankofaReads
ማንበብ ለምትወዱ ሁሉ
ሳንኮፋችን በስነ ጽሑፍ ዘርፍ የኖቤል ሽልማት አሸናፊ ጸሐፊያን መጽሐፍት ላይ ዳሰሳ መስራት አስባለችና ከዚህ ቀደም ከጸሐፊያኑ ያነበባችሁ ካላችሁ፣ለማንበብ ያሰባችሁና እንዲሁ ደግሞ ማንበብ ለምትወዱ ሁሉ አንድ አንድ መጽሐፍ በማንበብ ያነበባችሁትን መጽሐፍ ላይ ደግሞ አጭር ዳሰሳና ገለጻ በመስራት እንድትሳተፉ ሳንኮፋችን ትጋብዛለች።
በቅድሚያ ከታች የተዘረዘሩት ጸሐፊያንና የተመረጡ ጽሁፎቻቸው ላይ ቢሆን ይመረጣል። ካልሆነም እናንተው አንብባችሁ የወደዳችኋቸው(የኖቤል አሸናፊ ጸሐፊያን) መጽሐፍትም መሆን ይችላሉ።
1. Kristin lavransdatter : Sigrid undset
2. The last gift: Abdulrazak Gurnah
3. A farewell to Arms: Ernest Hemingway
4. The bridal canopy: Shumuel Yosef Agnon
5. One hundred years of solitude: Gabriel García Márquez
6. The stranger: Albert Camus
7. Beloved: Toni Morrison
8. The remains of the day: Kazuo Ishiguro
9. The books of Jacob: Olga Tokarczuk
10. As I lay dying: William Faulkner
11. The Immoralist: Andre Gide
12. Ake: Wole Soyinka
(ግጥም ለምትወዱ የ Rabindranath Tagore( Gitanjali), Pablo Neruda,Gabriela Mistral, Thomas Eliot, Wislawa Szymborska, louise glück, Octavio Paz ግጥሞች ላይ ዳሰሳ መስራት ትችላላችሁ)
የዳሰሳ ጽሁፉ በእናንተ አጻጻፍና ፍላጎት ስለሚሆን የመጻፍ ችሎታ የለኝም ብላችሁ እንዳትጨነቁ፣ለጓደኛችሁ ያነበባችሁትን እንደመንገር ዓይነት እንደሆነ አስባችሁ ተሳተፉ።
የሚሳተፉት የሁሉም አንባብያን ዳሰሳ ጭረት በተሰኘው የአንባብያን ማኅበሩ ዲጂታል መጽሔት ላይ የሚወጣ ይሆናል።
👉 Telegram: @sankofabooks Email: sankofareads7@gmail.com
#እናንብብ፣ እንለወጥ፣እናካፍል
ሳንኮፋ የአንባብያን ማኅበር
"እንጋባ" ሲል ጠየቃት አሳምነው። አልተቀበለችውም አስማሩ። "ወንድምና እህትነቱ ይበልጣል" አለችው። ተስማሙ።
ቤቷ እየመጣ ይጠይቃታል። ቡና ታፈላለች ይጠጣሉ፣ ካላት ታቀርባለች ይበላሉ። አወግተው ይለያያሉ። የትዳር ነገር ዳግም አልተነሳም።
አሳምነው አንድ ቀን በጠራራ ፀሀይ መጣ። እንደመጣ የደረበውን ሹራብ አውልቆ አስቀመጠ። ስለ ሙቀቱ ብዙ አውርተው ተለያዩ።
አስማሩ አሳምነው ረስቶት የሄደውን ሹራብ ልብሷን ስታጥብ አጠበችለት። ዳግም ሲመጣ ደርቦ ደራርቦ ነበርና የሚያወልቀው እንጂ የሚደርበው ልብስ አላስፈለገውም። ጃኬቱን አውልቆ ሄደ። አስማሩ እሱንም አጥባ አኖረችው። ሱሪውን ደርቦ መጣ "ወበቀኝ!" አወለቀው።
አስማሩ አጥባ አኖረችው፣ ካፖርቱን ጥሎ ሄደ፣ አጥባ አኖረችው። አንድ ቀን በጠራራ ፀሀይ ብርድ ልብሱን ለብሶ መጣ፣ አስማሩ "ምነው?'' አለችው። "በጠራራ ፀሀይ ብርድ ሆዴ ገባ'' አላት።
"ምች ይሆናል" አለችው። የምች መድኃኒት ብታሽለት ተሻለው። ሲሻለው ብርድ ልብሱ አላስፈለገውም ጥሎት ሄደ። አስማሩ አጥባ አኖረችው፡፡
ትንሽ ቆይቶ፣ ፍራሹን ተሸክሞ መጣ።
"ምነው?" አለችው።
"ላሳድሰው መሄዴ ነው። አይቼሽ ልለፍ ብዬ ነው'' አላት። አመነችው።
ጨዋታው ደራ፣ ፍራሹን ረስቶት ሄዶ ኖሮ እኩለ ሌሊት ቢመጣ አስማሩ ቦታ ስላጣች ፍራሹን ፍራሿ ላይ ደርባው ደረሰ። ያኔ "ተነሽ" ከማለት "ጠጋ በይ'' ማለት ቀልሎ ተገኘ። ጠጋ አለች::
By Alemayew Gelagay
@wegoch
@wegoch
@paappii
ደምበኛዋ ነኝ ፣ ደንበኛዬ ናት ያገልግሎት ገንዝብ ይሄን ያህል ነው ክፈል አትልም። ስንት ልክፈል ቀንሽልኝ አልላትም።
ሴተኛ አዳሪነቷን ላለማጉላት ነው ባደረች ቁጥር ክፈለኝ የማትለው? ሴተኛ አዳሪነቷን ላለማጉላት ይሆን በተኛን ቁጥር ስንት ነው ብዬ የማልከፍላት?
"የሆነ ብር አለህ እንዴ? ኪራይ መጣብኝ" ትለኛለች ያውም ብዙ ብር ነው ያለኝ ብዬ እሰጣታለሁ።
"ዛሬ አብረን እንሁን?" ስላት ብዙ ግዜ መልሷ እሺ ነው። የሴትነት ግዳጅ ላይ ብቻ አትሁን'ንጂ ቀጠሮ ቢኖራት 'ንኳ ትሰርዛለች...
ቀኑ 23 ከሆነም አትችልም።
"ታውቃለህ አይደል?"
ምኑን ዓይነት ስመለከታት...
"አንተን ማግኘት ብርታቴ እንደሆነ፤ ሴተኛ አዳሪነቴን ስለምታስረሳኝ፤ ታሪክ እንዳለኝ፥ ህልም እንዳለኝ አንተ ብቻ ነህ የምታስታውሰኝ!!"
ታውቃለህ ?
ዝምም ብዬ በትንሽ ፈገግታ ትክ ብዬ ሳያት...
እውነት እውነት ትላለች .....
ጠይም ናት፥ ቀጭን ናት፥ ሰልካካ ናት፥ ሁሉ ነገሯ ልከኛ ነው አብረን ተኝተን ነቅቼ አተኛኟን ሳየው ያሳዝናል
ሳለኝ ብላ የተኛች ሞዴል ትመስላለች።
"በ23 ለምን አሰሪም?" ስላት ከ23 ጋ ቁርኝት አለኝ 23 የኔ ቀን ብቻ ናት ትለኛለች።
አርፋለሁ!
"ሌላም ምክንያት ንገሪኝ?" ስላት "ሚስጥር ነው " አለቺኝ።
ሁሉንም አታወራም ስትከለክል ፈገግ ብላ ነው።
"ስወድሽ" አልኳት ...
"እምቢ" አለች ...!
ሁሌም ቤቴ ነው የምጠራት...ደርባባ ናት...ቆንጆ ናት። ቡርቴ ትባላለች ዐይኗ ጉልት ያለ ነው። ቤቴ ስትመጣ ተመላላሽ ሰራተኛዬ ሰትሠራ ያጎደችውን ትሞላለች፤ ያልጸዳውኝ ታፀዳለች። ወጥ ልስራ ምን ልስራልህ? ትላለች።
እንዴት አከበርኳት? እንዴት አከበረቺኝ? አላውቅም !
እንደዚህች ዓይነት ደርባባ እንዴት ሴተኛ አዳሪ ሆነች?
ገጠመኜን አወራታለሁ ትሰማኛለች ዕቅዴን እነግራታለሁ ትሰማኛለች አሰማሟ ምቾት ስላለዉ አወራለሁ ።
ብሶት እና እጦቴን ከራሷ አንፃር አይታ አታፅናናኝም በመረዳት በማዘን ነው የምትሰማኝ አሰማሟ እኔ የተሻልኩ ቦታ ላይ እንዳለሁ አይደለም !!
ሳማክራት ገላዋን በመሸጥ ለምትተዳደር በጣም ሲከፋት መጠጥ ውስጥ የተሸሸገች ሴት ምክር የምጠይቅ አልመስልም !
ሰው ባለበት ቦታ ብቻ አይመዘንም ኣ!
እንዋሰባለን ጡቷንም ከንፈሯንም ትፈቅድልኛለች። ወሲባችን የወንድ አዳሪ እና የሴት አዳሪ አይመስልም ትንሽ መዋደድ፥ ትንሽ መነፋፈቅ፥ ትንሽ ሕይወት ያለው ይመስለኛል ።
"ቡርቴ ለምን ሴተኛ አዳሪ ሆንሽ ?"
ሆኜ ነው ራሴን ያገኘሁት። መች እንደሆንኩ ቀኑን በትክክል አላውቅም ።
ዳዊት ነው ሴተኛ አዳሪ ያደረገኝ ። ዳዊትን ሳውቀው ዳዊት የተባለው ባጋጣሚ አይደለም አልኩኝ ። ምቹ እንደልቤ የሚባል ፍጡር ነው ።
እድሜ ይበልጠኝ ነበር
ትሁት ነው፥ ሃብታም ነው፥ ጨዋታ ይችላል፥ የማላውቃቸውን ውድ ሽቶዎች፥ የማላውቃቸውን ብራንድ ልብሶችና ውድ ጌጣጌጦች፣ ትላልቅ መዝናኛ ቦታዎች አሳየኝ። ዝነኛ ሰዎች ጋር አስተዋወቀኝ ።
ያስፈልጋታል የሚለውን ሁሉ ያደላድልልኝ ጀመር። ለቤተሰቦቼ መትረፍ ቻልኩ። ዳዊትን ከማግኘቴ በፊት የነበረኝ መርህ፥ አቋም ዕይታ ላላ። ዳዊት ሆነ የሚዘውረኝ...
ክብረ ንፅህናዬን፥ መንገዴ ዕይታዬ በዳዊት ተወሰደ...ከሃይማኖታዊ ስፍራ ራኩኝ ።
ቀስስ እያለ ውሎውን አዋለኝ። ውሎውን ለመድኩ። መጠጥ ለመድኩ። ማጨስ ለመድኩ...
የሆነ ቀን አንዲት ማድያት ያለባት ዕድሜ የምትበልጠኝ ቆንጀ መልከ መልካም መጥታ "ከትዳሬ ውጪልኝ አለቺኝ.... "
ስለምን እንደምታወራ አልገባኝም ነበር። ዳዊት ባለትዳር እንደሆነ ሦስት ልጆች እንዳሉት ከብዙ አባሪ ጋ አሳየቺኝ...
ለካ ቅምጡ ነበርኩ...
ስታወራኝ ብዙ ነገሬ በድን ሆኖ ነበር። ድንግጥ አልኩ ! ህልም መስሎኝ ነበር! ፈርቼ ነበር! አደባባይ ላይ እርቃን እንደ መቆም ዓይነት ስሜት ተሰማኝ። የሚያደርግልኝ ነገር ሁ፥ የሚያሳየኝ ነገር ሁሉ ግዚያዊ ነገር ብቻ ነበር።
ያወራናቸውንና የተላላክናቸውን የፅሁፍ እና የድምፅ መልዕክቶች በረበርኳቸው፤ ሁሉንም !! አንድም ስለ ልጆቹ፥ አንድም ስለሚስቱ ያወራልኝ ቦታ ሳላገኝ ቀረሁ።
የመጣንባቸውን መንገዶች፥ ሁኔታዎች ሳሰላስላቸው እንቅስቃሴው እና የሚወስደኝ የምናወራው ነገር ሁሉ ቅምጡ እንደ ነበርኩ ምልክቶች ነበሩት ።
አንዴንዴ የሚታይ ነገር መመልከቻችን ይታወራል !! ለሁሉም የሚታይ ነገር ለኛ ይሸሸጋል!
ዳዊት ዐይኑን በጨው አጥቦ ሌላ ማልያ ለብሶ መጣ። እንደገና ሌላ ማሳመኛ ይዞ መጣ።
ይሄን ያህል ደደብ ነው የምመስለው?? እንደገና ሌላ ሃዘን አጠቃኝ...
ጓደኛው አፅናናኝ ...
ወቀሰልኝ... አብሮኝ ቆመ... ተቆረቆረልኝ...አለሁልሽ አለኝ...አብሮኝ ሆነ...በዳዊት ቦታ በሂደት ተካኝ። ጓደኛ ሆኖ መጥቶ ቅምጥ አደረገኝ።
ሌላ አገር ሄደ ...
ሌላ እሱ ያስተዋወቀኝ ጓደኛዉ ቢዝነስ ሊያስጀምረኝ ቃል ገብቶልኝ ስናወራ ስንግባባ ስናወራ ስንውል ስናመሽ በሂደት ራሳችንን አልጋ ላይ ማግኘት ጀመርን።
የሆነ ቀን ለከፈለኝ ሁሉ ቀሚሴን ስገልብ እራሴን አገኘሁት። ለራሴ ያለኝ ክብር በሂደት ተሸረሸረ ።
ለከፈለኝ ሁሉ እርቃኔን የማሳይ ሆንኩ፣ ከከፈለኝ ሁሉ ጋ እተኛለሁ ።
ብዙ ግዜ ራሴን ላጠፋ አስቤ አውቃለሁ።
ምን ያዘሽ?
ተስፋ ... !
የማውቃቸው ሴተኛ አዳሪዎቹ ሲያልፍላቸው፤ ሲያገቡ ሲያምርባቸው ተስፋ አደርጋለሁ!! የወደቀ ሲነሳ ስመለከት ተስፋ አደርጋለሁ!
ያጣ ሲያገኝ ሳይ ተስፋ አደርጋለሁ! በየደረጃችን ተስፋ ላይ ሙጥኝ ብለን የምንልወሰወስ ፍጡር ነን አይደል?!!
ቡርቴ?
ወዬ
ምን መሆን ትፈልግያለሽ ?
ብዙ ነገር! ግን ሁሉም ዕቅዴ ውስጥ ከሴተኛ አዳሪ ሕይወት መውጣት የሚል አለ።
By Adhanom Mitiku
@wegoch
@wegoch
@paappii
ስለዚህ እንከን አልባ ሰው በመፈለግና ያገባሽውን ሰው እንከን ለማጥፋት በከንቱ ከመዳከር ይልቅ ከእንከኑ በላይ እወደዋለሁ ከምትይው ሰው ጋር ተጣምሮ ለመኖር የሚወሰንበት ጉዳይ መሆኑን አምነሽ ግቢበት።
አለ አይደል…
ይህችን እስስት ዓለም ብቻዬን ከምፋለማት አብሮኝ ቢሆን ሸክሜን ያቀለዋል የምትይውን፣ ሲከፋኝ ጀርባዬን በመዳፉ ቸብ ቸብ ያደርግልኛል፣ ሳለቅስ እምባዬን ይጠርግልኛል የምትይውን ሰው ባል አድርጊ።
ይሄው ነው። ከዚህ የረቀቀ፣ የተወሳሰበ ጉዳይ የለውም።
ውይ…ረስቼው…
እቱ ገላ!
አደራሽን ይህችን እንዳትዘነጊ! ከትዳር በፊት ያለውን ነገር ስታደርጊ…በገርልፍሬንድ ማእረግ ሚስት ሆነሽ እንዳትገኚ! በእጮኝነት ዘመንሽ የሚስትነት ሃላፊነትን አትረከቢ፡፡
By hiwot emishaw
@wegoch
@wegoch
@paappii
የኔ እህት አዚህ ሰፈር ነሽ?
(አሌክስ አብርሃም)
አንድ የሰፈራችን ባለሱቅ የሆነ ቀን በበሩ ሳልፍ "ወንድሜ" ብሎ በአክብሮት ጠራኝና እዚህ ሰፈር ነው የምትኖረው? ብሎ ጠየቀኝ! "አወ" አልኩት እንዴት ረሳኝ ብየ በመገረም! የረዢም አመት ደንበኛየ ነበር። ቀጠል አድርጎ
ሲጃራ ታጨሳለህ እንዴ?
አይ አላጨስም
አቁመህ ነው?
አይ ከመጀመሪያውም አላጨስም
ጫትስ ትቅማለህ እንዴ?
አይ አልቅምም
አቁመህ ነው?
ቅሜ አላውቅም! ለምንድነው ግን የምትጠይቀኝ አልኩ ገርሞኝ ። ጥያቄየን ችላ ብሎ
እ...የስልክ ካርድ ከኔ ትወስድ ነበር እንዴ?
አወ (ደግሞ እውነቴን ነው ከሱ ሱቅ ነበር የምገዛው)
ባለስንት ነበር የምትገዛው?
ባለመቶም ፣ ባለ ሃምሳም ...ባለ ....
ተወው አስታወስኩ! የመቶ ብር ካርድ አለብህ ስምህን መዝገብ ላይ አይቸዋለሁ
ማነው ስሜ ?
ስምህ ምን ያረጋል ጋሸ? ዋናው ካርዱ ነው ....😀
በኋላ ስሰማ ይሄ ሚስኪን ባለሱቅ አእምሮውን ታሞ አማኑኤል ሆስፒታል ገብቶ ነበር አሉኝ። ሚስቱን ነበር ሱቁ ውስጥ ለረዢም ጊዜ የማያት! እና ዘለግ ላለ ጊዜ ታክሞ ከአማኑኤል ተሽሎት ወጣ። ሁሉ ነገር ተስተካክሎ አንድ ነገር ብቻ ትንሽ ልክ አልመጣለትም እየተባለ ይወራል። ማንኛውም በሱቁ በር የሚያለፍ ሰው ዱቤ ወስዶ ያልከፈለው ይመስለው ስለነበር እያስቆመ አጭር መስቀለኛ ኢንተርቪው ያደርጋል። ከምንም በላይ ግን ያሳቀቀን እትየ ማርታን ጠርቶ ጠየቃት የተባለው ነገር ነው። እትየ ማርታ ዕድሜዋ 40 የተሻገረ ዘናጭ ሴት ናት!
"እህቴ ይቅርታ እዚህ ሰፈር ነሽ?" አላት
አወ ምን ልርዳህ? አለች በሚያምር ፈገግታ
ፔሬድ ማየት አቁመሻል እንዴ ወይስ ታያለሽ ? አበደች ...
"ስድ ምናባህ አገባህ?" በኋላ ባሏ ተነግሮት ሊያናፍጠው ወደሱቁ ሲሄድ "ሞዴስ በዱቤ ወስዳ ያልከፈለችኝ መስሎኝ ነው ጋሸ ! ግን ከመጣህ አይቀር ታጨሳለህ እንዴ.....😀"
@wegoch
@wegoch
@paappii
ሌላ ሴት ልታገባ ያልክ ቀን እንኳ ብደውልልህ እሷን ትተህ እኔ ጋር ነው አይደል የምትመጣው? እለዋለሁ ሁሌ …. ፈገግ ብሎ ያየኝና “ደፋር ኮ ነሽ….ይለኛል።
ካለሁ ነገር ሁሉ እኔን አስበልጦ እንደሚወደኝ አውቃለሁ። ሲሳሳልኝ:ከራሱ ሲያስቀድመኝ: ሲጨነቅልኝ: ለኔ ሲኖር አይቻለሁ። ( በእርግጥ እንዲ ማለት ከባድ ይመስላል። እኔ ግን አይኑን ሳያርገበግብ : ይሄን ልጅ ግን ምን አስነክታው ነው እስኪባል የሚያውቁን ሁሉ እስኪገረሙ ድረስ ….ሳናድደዉ :ሳበሳጨው ችሎ በክፉ ቀናቶቼ ላይ ለደስታዬ ሲፈጋ: አብሮነታችንን ለማቆም ብዙ ሲለፋ አውቅ ነበር።)
ይመስለኛል የበዛ መውደዱ: የትም አይሄድም ብዬ እንዳስብ ለኛ እንዳልጨነቅና በተወዳጅነት ተኮፍሼ ለሚሰጠኝ መውደድና ክብር ትንሽ እንኳ አፀፌታን መስጠት የማልችል ሴት አደረገኝ።
ከዛ በአንዱ ቀን በትንሽ ነገር ተጋጨንና ….ሂድልኝ አልኩት። ለመነኝ:አስለመነኝ….ከቀልቤ መሆን ያልቻልኩት እኔ ግን ግድ አልሰጠኝምና ምንም እንደጎደለብኝ አልተሰማኝም። መሄዱ እንደሚያም: እንዴት እንደሚናፍቀኝ ለመረዳት ብዙ ረፈደብኝ።
ሄደ። ከዛ አልተመለሰም። ልመልሰዉ ሞከርኩ….መሄድ አለማምጄው ኖሮ መመለስ አቃተኝ።
እናማ አሁን የገፋሁት እኔ: ወዶኛል አይጠላኝም ያልኩት እኔ: በተራዬ እጅግ እየናፈቀኝ:እያመመኝ :እያስመሰልኩ አብሮነታችን ማክበር ያልቻልኩት እኔ … ሲያቅፈኝ ህይወት እንደሚቀለኝ: ችግሮቼን ችሎ ማሸነፍ ብቻን ያለማመደኝ እሱ እንደነበር:በጣም እንደሚናፍቀኝ :በጣም እንደማመሰግነው ያልነገርኩት እኔ የሄደበትን ቀን ሻማ እያበራሁ አከብራለሁ።
በስመአብ ጊዜው እንዴት ይሮጣል? አትመጣም በቃ?
By Ma Hi
@wegoch
@wegoch
@paappii
አልጣሽ
ገፃቸው በመታከት ዳምኗል።አይኖቻቸውን ቡዝዝዝዝ አድርገው ፊትለፊታቸው የሚነታረኩትን የልጅ ልጆቻቸውን በአርምሞ ሲያዩ ከቆዩ በኋላ "አይ አለመታደሌ!" ብለው በረጅሙ ተነፈሱና እያዘገሙ ወደ ኩሽናው ዘለቁ። ተንበርክከው የምጅጃውን እሳት በእፍታ የሚታገሉትን ባለቤታቸውን በጨረፍታ ቃኝተው አለፉና መደቡ ላይ በቁማቸው ወደቁበት።
አያ ቢምር እና እመይቴ አልጣሽ በስተርጅና የልጅ ልጆቻቸው ሞግዚት ሆነው የአፍታ እረፍት የሰማይ ያህል እንደራቃቸው ውለው ሌላ የድካም ቀን እስኪመጣ ያሸልባሉ።የመጀመሪያ ልጃቸው ሁለቱን የእራት አመት መንታ ልጆቿን፣ሁለተኛው ልጃቸው ደግሞ እህል በአፏ ከሌለ አርፋ የማትቀመጠዋን የሁለት አመት ልጁን ጥለውባቸው ወደ አጨዳ ያቀናሉ።
"እመይ...አበይ...ደኅና አድራችኋል?ንሱ ልጆይን ፍቀዷቸው...ህደናል" ይሏቸዋል።
ዛሬም እንደወትሯቸው ሶስቱ ህፃናት የወላጆቻቸው ዳና ከመጥፋቱ እየተፈራረቁ ጎጆይቱን በአንድ እግሯ ያቆሟት ጀመር።መንትዮቹ ፍቅሩ እና ሰውነት ከውልደታቸው አንስቶ ተስማምተው አያውቁም።እንደውም የቆዬው የልምድ አዋላጅ "አይ ሰውነት!ያኔም የእናታቸው ምጥ ሲመጣ...ወይ እሱ አይወጣ...ወይ ወንድሙን አያስወጣ...አናቱን በእግርና በእግሩ መሃል ደፍጥጦ ይዞ ብርሌ አስመስሎት ቀረ...ይኸው አድጎም አልተወው"ይላሉ መንትዮቹ ሲጣሉ ባዩ ቁጥር።ረፋዱ ላይ እመይቴ አልጣሽ ያቀጠኑትን ሊጥ ተሸክመው ወደ ምጣዳቸው አቀኑ።ሊጡን በኩባያ እየጠለቁ እንደ ረሀብተኛ ልዥ ሆድ መሃሏ የጎደጎደው ምጣዳቸው ላይ ያፈሱትና በክብ ቅርፅ በተሰራችው የጣውላ ማለስለሻቸው ዙሪያዋን ያለብሷታል።እንደ ሽማግሌ ጥርስ ዙሪያው የተፈረካከሰ ሙግዳቸውን አንስተው ምጣዳቸውን ከመክደናቸው ሰውነት ሲከንፍ መጥቶ ሊጡ ላይ አንድ ጆግ ውሃ ይሞጅርበትና እያሽካካ ይሮጣል።የ 80 አመት ጉልበታቸው አሯሩጦ መያዝን ባይፈቅድላቸው
"ሃይ!...ሃይ!...ሃይ!...ምነ ምነ አንዳች ያልታሰበ ቢያጥለቀልቅህ!"ረግመውት ወደ ሊጡ ይዞሩና
"አይ አለመታደሌ!"ብለው ከጎን ያለው ምድጃ ላይ አብሲት ሊጥዱ ገለባ መማስ ይጀምራሉ።ከእሳት ጋር ሲታገሉ አልፈዋቸው ከመደቡ የወደቁትን ባለቤታቸውን እየቃኙ
"ይኸ ተንከሲስ... ሊጡን አቅጥኖ አፈር አልብሶኝ አያ ቢምር!...አብሲት እስክጥል ማታ ከድኘ ያኖርኳት ሞሳ ባጨላ አለች በሳህኔይቱ...ይህዱ ጓዳ እሷን እየቀመሱ ይቆዩኝማ" ብለው አባብለው አሰወጧቸው።አያ ቢምር በጋሬጣና በእንቅፋት ጥፍሮቻቸው የወለቁ እግሮቻቸውን እየጎተቱ ወደ ጓዳ አቀኑ።መሃል ወለል ላይ ትንሿ የልጅ ልጃቸው በሁለቱም ጉንጮቿ ሞልታ የምታኝከው ባቄላ መፈናፈኛ አሳጥቷት በጭንቅ ስትቃትት አገኟት።ከ60 አመት በላይ ሞፈር የታዘዘለት እጃቸውን ወደ ማጅራቷ ሰደው መሬትን በአፍንጫ አስልሰው ካቃኗት በኋላ
"ኧረ አፈሩን ብይው!ይችን የመጋዣ ልጅ መጋዣ! "ሲሉ ተራግመው እመይቴ አልጣሽ የጠቆሟቸውን ሳህን ሲያማትሩ ከአጠገቧ እርቃኑን ተቀምጦ አዩት።እጆቻቸውን ወደላይ ሰቅለው
"አይ አለመታደሌ!" ካሉ በኋላ እንደ አመጣጣቸው እያገዘሙ ወደ ባለቤታቸው ተመልሰው መደቧ ላይ ተጠቅልለው ተኙ።
እንጀራና ወጡ ተዘጋጅቶ የምሳ ወጉ ከደረሳቸው በኋላ አያ ቢምር ከልብ ወዳጃቸው ጋር ሊያወጉ ወደ መንደር ዘለቁ።እመይቴይቱ ግን ፣ ቁሞ በመዋል የተብረከረኩ ጉልበቶቻቸውን ታቅፈው፣እሳት ያሟሸሻቸውን አይኖቻቸውን ከመክደናቸው እዛው ኩሽናው ወለል ላይ እንደተጋደሙ የልጅ እንቅልፍ ወሰዳቸው።ለአፍታ ካሸለቡ በኋላ ከአለት የከበደ አንዳች ነገር ጆሯቸውን ሲጫናቸው እየጮኹ ተነሱ።ዙሪያቸውን እየተፈራረቁ ከሚስቁት ሶስት ህፃናት ጋር እላያቸው ተበግራ የቆመችዋን ጥጉቧን አህያቸውን እያባረሩ የተረገጠ ጆሯቸውን በሻሻቸው ጥፍንግ አድርገው አስረው እዬዬአቸውን ያወርዱት ጀመር።ፍቅሩ ፈገግታው ከገፁ ሳይጠፋ እየተጠጋቸው
"እመይ...ሰውነት'ኮ ነው የኩሽናውን በር ከፍተን አህያይትን እናስገባትና ምጣዱን ትስበረው ያለኝ"አለ ወንድሙን በስርቆሽ እያየ።
"ይሄይ?ይኸ?ይኸማ ቢሆንለት በተኛሁበት ቢያነደኝ ነበር ደስታው...ምነ አንተ ዝም ያልከው እንግዲያ?"
" 'አፍርጨ ነው የምጥልህ' እ...እያለኝ"
"ፈ...ርጠህ ቅር በለ...ው እንደ እ...ንቧይ"ከማለታቸው በተረገጠው ጆሯቸው በኩል አንዳች ነገር 'ጭውውውውውውው' ሲልባቸው ታወቃቸው።
አመሻሽ ላይ ተረኛው እረኛ ታሪክ
"እመይቴ አልጣሽ....ከብቶይን አምጥቻቸዋለሁ አስገቧቸው" ብሎ ጮኸና ምላሻቸውንም ሳይሰማ ወደሌሎች ባለከብቶች አቀና።
አያ ቢምር ከዋሉበት ወግ ሲመለሱ መንትዮቹ እንደወትሯቸው እየተነታረኩ፣ትሁንም ከምሳ አትርፈው የከደኑት መሶብ ላይ ለብቻዋ ሰፍራ እየታገለች፣ከብቶቻቸውም የጎረቤታቸው ማሳ ላይ ሲምነሸነሹ አገኟቸው።ከብቶቹን ከበረታቸው ጨምረው ባለቤታቸውን ጥሪ ገቡ።
"አልጣሽ!...ኧረ አልጣሽ!ኧረ 'ምኑ ገባሽ?"እያሉ ዋናውን ቤት ቆጡ ሳይቀራቸው አሰሱት።እየተጎተቱ ወደ ኩሽናው ሲዘልቁ እመይቴ አልጣሽ እጥፍጥፍ ብለው ተኝተዋል።
"ኧግ የደረባኑ መልአክ!ምነ አልጣሽ ምነ?አስርና ክያ እነጀራ አወጣሁ ብለሽ እስካሁን መኝታ?ኧረግ የኔይቱ ወይዘሮ!"ብለው እላያቸው ላይ ጣል ያረጉትን ኩታ ሲገልጡት አፀድ የመሰለው ሻሻቸው በደም ርሶ፣የጆሮ ግንዳቸውና የአንገታቸው ስር የደም ድልህ ተጋግሮበት አገኙት።ያዩትን ስለተጠራጠሩ ኩታውን ወደነበረበት መልሱና አይኖቻቸውን ማሻሸት ገቡ።ፍቅሩ ሲበር መጣና
"አበይ...ይኸ ሰውነት እመይን በተኛይበት ጥጉቢትን አህያ አስረገጣት።ጥሩ ውሃ ስጭኝ ብየ ብጠራት ብጠራት አኩርፋ ነው መሰል ዝም አለችኝ።ናማ አንተ ስጠኝ"
የእመይቴ አልጣሽ ቀብር ላይ አንድ ወዳጃቸው እንዲህ ሲሉ ሙሾ አወረዱላቸው።
"አንች የኔ ጉልበታም እንዲህ ነበርሽ ወይ
ክያ እንጀራ አውጥተሽ ማረፍሽ ነወይ
አንች ተደከመሽ እኔ እጋግራለሁ
ጠጅሽን ያሉ እንደሁ እንዴት አደርጋለሁ
ቀና በይ አልጣሽ ቅጅልኝ ከጠጁ
የጠላሽ አይጠፋም ሞልቷል የልጅ ልጁ"
ዘማርቆስ
(@wogegnit)
@wegoch
@wegoch
@wegoch
አባቴ ካጠገቡ የማትጠፋ ራዲዮ ነበረችው። ኹለት ስፒከር አላት ካሴትም ታጫውታለች...
ፀሐይ በራኺን አስሬ ይሰማታል። አክስቴ ትመስለኝ ነበር፤ ድምጿ እኛ ቤት አይጠፋም ስትዘፍን እኩል እላለሁ ከሙዚቃው ጋር...
"መጀመርታ ፍቅሪ
ኣብ መን ተጀመረ
ኣዳምን ሔዋንን
አለም ምስተፈጥረ
ኣነ ከይፈለጥኩ
አብ ልበይ ሐደረ
እንታይ እሞ ክገብር
ዕድለይ ካብ ኮነ አይ..አይይ*
አባቴ ወታደር ነበር። ጠይም ነው መከፋቱ ፊቱ ላይ ብዙ አይታይም፤ ማጣቱ በየምክንያቱ አንደበቱ ላይ አይንፀባረቅም ....ዝምም ይላል
ረጋ ያለ ነው ።
ጥርሱን ሳያሳይ ነው ደስ ብሎኛል ፈገግታ ፈገግ የሚለው፤ ተገርሜያለሁ ፈገግታ ፈገግ የሚለው ተበድያለሁ ፈገግታ ፈገግ የሚለው አጠገቤ ሲሆን እረጋጋለሁ።
ሰሞኑን ሰውነቴ እንደከሳ፤ ፊቴ ማዘን እንደታከከው፤ ድብርት ነገር እንዳንጃበበብኝ አወቀ። አባትም አይደል? ንብረቱም አይደለሁ? ዋጋ ከፍሎብኝም የለ?
ፊቴን አይቶ "ደህና ነህ ህሉፌ ...?" አለኝ።
'እ ...ትንሽ ደከመኝ...
አሻግሬ ማየት እያቃተኝ... ቶሎ ቶሎ እጅ እየሰጠው ..." አልኩት።
ረጅም ሰዓት ዝም አለ ...
"ታስታውሳለህ በረሃ እያለሁ የምፅፍላችሁ ደብዳቤ፤ በርቱልኝ፥ ምን ጎደላችሁ፥ እወዳችኋላሁ፥ በቅርብ እደውልላችዋለሁ፥ እመጣለሁ፥ ዓይነት ይዘት ያለው ፅሁፍ ?! ።"
"ባሩድ እየሸተተኝ ነበር፥ አብሬው የዋልኩት ጓደኛዬ ሞቶብኝ፥ ፍንጣሪ ጥንት መ'ቶኝ፣ ጠላት ሊፈጀን እያቀደብን፣ ጀኔራላችን ምሽግ ሰብራችሁ ግቡ ሊለን እንደሚችል እያወቅን፥ የተቀበረ ቦንብ ልንረግጥ እንደምችል እያወኩ፥ ከአውሮፕላን የተወረወረ ፈንጅ ሊያወድመን እንሚችል እያወኩ፥ ነበር...አሻግሬ ተስፋ የማየው..."
ፋታ ወስዶ ቀጠለ...
"ልጆቼን እንደማገኛቸው፥ አባት እንደምሆንላቸው፥ ሚስቴን ዳግም እንደማገኛት ፤ቤተክርስትያን እንደምሳለም የፈንጂ ድምፅ ሳልሰማ እለት እለት የወደቀ ሬሳ ሳልሻገር እንደምኖር ተስፋ አደርግ ነበር ...
ስለመግደል የሚታቀድበት ስፍራ ላለመሞት የሚዘየድበት ቦታ አንድ ቀን እንደማልኖር አምን ነበር ...!
ተስፋን ሙጥኝ ብዬ ነው ዛሬን ያየሁት ። ያጋጠመኝን መውደቅ እና ሃዘን ህመም ችላ ብዬ ነው ያን በርሀ የተሻገርኩት !!
አጆኻ ዝወደይ ..
ሁሉም ሰው መስቀል አለው ልዩነቱ አይነቱ እና አሸካከሙ ነው !!"
By Adhanom Mitiku
@wegoch
@wegoch
@paappii
የሆነ ሰዓት እሽኮለሌሌሌ ያሉ ጥንድ ጓደኞች ነበሩኝ። ነገራቸው ሁሉ እንዳይሆን እንዳይሆን ነበረ(እንኳንም ትለያያላችሁ የምንለው አይነት😅)
ከዛ በቃቸው መሠለኝ በአሪፍ ፀብ ተጣሉ ፥ በመኻል የእሱ እናት ሞተች።
ኧረ ይደብራል መኼድ አለብሽ ምናምን ብዬ ሰባብኬ በሰልስቱ ይዣት ሄድኩ ።
ወግ ነው መቼም ብላ ጠጋ ብላ "እንዴት ነህ በረታህ ?" ስትለው ምን አላት :-
"ሀዘኔን ልትቀሰቅሺብኝ ነው ከተፅናናሁ በኋላ የመጣሽው ?" 😂
By beza wit
@wegoch
@wegoch
@paappii
አደፍርስ
አብዬ አደፍርስ የሚስታቸውን ግልምጫ ያመልጡበት፣የልጆቻቸውን ሆድ ይሞሉበት መላው ቸግሯቸዋል።የዛሬ አራት ወር ገደማ በጥበቃነት ይሰሩበት የነበረው ባንክ የዘረፋ ሙከራ ተደርጎበት የነበረ ጊዜ ዘራፊዎቹን በጉልበታቸው መመከት እንደማይችሉ ሲያውቁት በድረሱልኝ ጥሪ ቢዘርሯቸውም የባንኩ ማናጀር እሳቸውን አባሮ በቦታቸው ከሳቸው በእድሜ አነስ የሚል ጎልማሳ ከመቅጠር ወደኋላ አላለም።ይኸው ከተባረሩ አንስቶ ሁሌ ማለዳ ማለዳ ከስራ ሰዓት ቀደም ብለው ያደረ ሽንታቸውን ከቤት ይዘውት ይወጡና ባንክ ቤቱ አጥር ስር ሲደርሱ ነው ቀበቷቸውን የሚፈቱት።
ስጋ ለበስ ብትራቸውን አራግፈው ከሱሪያቸው ስር እየወሸቁ
"ኡኡ ባልኩ?እንደ ሴት ጮሄ ባስጣልኩ?" ይላሉ።አሁን አሁን ግን ረሀቡ ጠናባቸው።የሶስት ልጆቻቸው አንጀት እግርና እግራቸውን ተብትቦ ይዞ አላራምድ አላቸው።ሚስታቸው ከጉሊት ውለው ሲመጡ ከሬሳ የከረሰሰ ሽሮ ያቀርቡላቸውና
"አንቱ የሴት ገንዘብ ምን ምን ይላል?እስቲ ቀምሰው ይንገሩኝ" ይሏቸዋል።
ሁለመናው ከትዕግስታቸው ቋት እየፈሰሰ አልሆን ሲላቸው ሂሩትን አማከሯት...የመንደራቸውን አድባር።ሂሩት በመንደሩ ብቸኛዋ አጭር ቀሚስና ሂል ጫማ የምትለብስ የመንግስት ሰራተኛ ናት።እንዳማከሯትም አላሳፈረቻቸውም ማንበብና መፃፍ የሚችል ሰው ሁሉ ሊሰራው የሚችል ስራ አገኘችላቸው።አላምናት ብለው
"አየ ሂሩት...ይኸን ሽማግሌ ልቀልድበት ብለሽ ነው መቸም"
"አባቴን ይንሳኝ የምሬን ነው!"
"እንዴት ያለ ነው ስራው?"
"አልጋ ቤት ነው የሚሰራው አብዬ...አንድ ቀን በቀን ፈረቃ ሌላ ቀን በማታ ሆኖ አልጋ የሚይዘውን ሰው መታወቂያ ይዘው ስም እየመዘገቡ ብር ተቀብሎ ማሳደር ነው።የማታ ሲሆኑ ማደሪያዎትን ቆንጆ አልጋ ይዘጋጅልዎታል።"
"አልጋ ቤት?"አሉ ቅሬታ በተሞላ ድምፀት።
"አዎ...መንገደኛና የሰው አገር ሰዎች...ነጋዴዎች አልጋ ተከራይተው ሲያድሩ እነሱን መመዝገብ ነው አብዬ።"
"እንዴት ነው እነሱ ተኝተው እኔ ስጠብቃቸው ላድር ነው?ተይ ተይ ቤቱን ዘርፈውት የሄዱ እንደሁ በጉዴ እወጣብሻለሁ ሂሩቴ"
"ኧረ ቤቱ የራሱ ጥበቃ አለው!የርስዎ ስራ መዝግቦ መተኛት ነው"ስትላቸው እያቅማሙም ቢሆን ተስማሙ።
የመጀመሪያውን ቀን በቀን ፈረቃቸው አቀላጥፈው ሰሩ።ይጠፉብኛል ብለው የፈሯቸው ፊደላት ሁሉ እንደ ይስሐቅ ታዘዟቸው።ያሞጨሞጩ አይኖቻቸውም የዋዛ አልነበሩምና ከየሰዉ መታወቂያ ላይ ጥቁሩን ከቀዩ፣ጠይሙን ከቀይ ዳማው አበጥረው ለዩት።አመስግነው ቤታቸው ሲገቡ ባለቤታቸው ከወትሮው በተለየ በትኩስ ሽሮ ተቀበሏቸው።አቦል ይሁን በረካ ባይለይም ቡና ተፈልቶላቸው አንድ ሲኒ ጠጡ።ለወትሮው ጀርባቸውን ይሰጧቸው የነበሩት እመይቴ አማረች ጡትና ጡታቸው መሃል አስተኝተው ራሳቸውን ሲዳብሷቸው አመሹ።
በሁለተኛው ቀን በማታ ፈረቃቸው ሰዓታቸውን አክብረው ተገኙ።አንድ ሶስት መንገደኞችን መዝግበው ቁልፍ ከሰጡ ወዲያ ሁለት ወጣቶች ተቃቅፈው መጡና አጠገባቸው ቆሙ።ሲታዩ እድሜአቸው እምብዛም አይራራቅም።ሴቲቱ ከማውራት ይልቅ ፈገግታና መሽኮርመም ይቀናታል።ወንዱ የጤና በማይመስል ሁኔታ ይቁነጠነጣል...ችኩል ችኩል ይላል።
"እ ፋዘር...አልጋ አለ ኣ?"
"አለ...ሁለት ነው አንድ የፈለጋችሁ?"
"ኧረ ቆጥበን እንጠቀማለን ሃሃሃ...ባለ አንዱ ስንት ነው?"
"ሁለት መቶ ብር"
"ሁለ'መቶ?" አለና ግንባሩን ክስክስ አድርጎ አጠገባቸው ያለውን አልጋ እያየ
"እንደዚህ ነው እንዴ አልጋው?"ጠየቀ።
"ኧረ ይች የኔ የብቻየ ስለሆነች ነው...ውስጥ ያለው ሰፋፊ ነው"አሉ እያፈሩ።ልጅቷ የልጁን ጎን በስስ ቦክስ ነካ አርጋ በዝግታ "አንተ አታፍርም?"ትላለች።
" ሀዬ በቃ መዝግቡና ፋዘርዬ" አለ መታወቂያውን ፍለጋ ኪሱን እያመሰ።ወዲያው ነገር በድንገት ብልጭ እንዳለለት ሰው እያደረገው
"ውውውውውይ በናትሽ!...ለካ አይ.ዲ.ዬን ያ ዘበኛ እንደያዘው ነው...ያንቺን አምጪው በቃ" ሲላት ቅር እያላት መታወቂያዋን አውጥታ ሰጠች።አብዬ አደፍርስ ፎቶዋን አበጥረው አዩና ወደ ስሟ ወረዱ።ለአፍታ ከመረመሩት በኋላ የሚያውቁት ፊደል ሲያጡ ቀና አሉና።
"ማነው ስምሽ"? አሉ።
"የኋላ'ሸት"
"እና ምነ በአማርኛ ቢፃፍ?" አሉና ስሟን ሊመዘግቡ ፊደላቱን ከአዕምሯቸው ጓዳ ያተራምሷቸው ጀመር።እየተንቀጠቀጡ ስሟን ፅፈው ሲጨርሱ
"የአባትሽስ?"
"ይበልጣል"
አሁንም እየተንቀጠቀጡ ሊመዘግቡ ሲያቀረቅሩ ልጁ ትዕግስቱ ተሟጦ
"ፋዘር እኔ ልመዝግበው የፈጠነ?"
"እ?"
"የፈጠነ...እኔ ፃፍ ፃፍ ላርገው?"
"ቆይ እስቲ...ይ...በ...ል...ጣ...ል...ይበልጣል"አሉና ቀጠል አርገው
"ስራ?"
"ተማሪ ነን"
"ተ...ማ...ሪ...ተማሪ"ይህንንም በዘገምታ አስፍረው ስልክ ቁጥር ከመዘገቡ በኋላ ክፍያ ተቀብለው ቁልፉን አስረከቧቸው።ለክፋቱ የዚያን ቀን የቀረው ብቸኛ ክፍል ከሳቸው ምኝታ ቤት ቀጥሎ ያለው ነበር።
አገር አማን ብለው ሊያሸልባቸው ሲል ከመሬት መንቀጥቀጥ ያልተናነሰ መናወጥ ከሰመመናቸው አባነናቸው።ተገስ እስኪል ጠበቁና ወደ ክፍሏ በር ጠጋ ብለው አንኳኩ።
"የኔ ልጅ"
"ምንድነው ፋዘር?"
"እንደው አደራህን የኔ ዓለም የአልጋው ብሎን እንዳይረግፍ...ደሃ ነኝ የምከፍለውም የለኝ...ወይ ፍራሹን ታወርዱት"?
"ሀዬ በቃ ይወርዳላ!"
ወደምኝታቸው ተመልሰው ፀሎታቸውን እያነበነቡ በድጋሚ ሊያሸልባቸው ሲል የድረሱልኝ ጥሪ የሰሙ መስሏቸው ብርግግ ብለው ተነሱ። ጆሯቸውን ቀስረው ሲያዳምጡ ጩኸቱ ከጎረቤት ነው።ጭንቅ ሲላቸው የስልካቸውን ራዲዮ ከፍተው ወደ ጆሯቸው ለገቡት።
"እንግዲህ አድማጮቻችን ከምሽቱ 12:00 የጀመረው የመዝናኛ ዝግጅቻችን እንደቀጠለ ነው።በያላችሁበት እጅግ ያማረ ጊዜን እያሳለፋችሁ እንደሆነ አንጠራጠርም።ታሪኳ ይነበብ ከሞጣ 'አትጠገቡም' ብላናለች።...ሆዴ ሞላ ከደጀን...እግዜሩ ባይከዳኝ ከጎንደር...ብርአልጣ ዘለዓለም ከማርቆስ 'ዝግጅታችሁ ተወዳጅ ነው' ብለውናል።ከኤፍሬም ታምሩ ሙዚቃ በኋላ ተመልሰን የምንገናኝ ይሆናል።አብራችሁን ቆዩ"
"...ወይ ዘንድሮ(2X)...ወይ ዘንድሮ(2X)
ወይ ዘንድሮ አያልቅም ተነግሮ"
ሙዚቃው ሲያልቅ የስልካቸውን ራዲዮ እየዘጉ
"ወይ የአንት ያለህ!!!እንዴት ያል ዘመን መጣብና?ወንዱ እንደ ሴት እየጮኸ? ኧረግ የእንድማጣው!ቱ!ቱ!ቱ! ሞት ይሻል የለም ወያ አንድ ፊቱን!"እያሉ ይብሰለሰሉ ጀመር።ለሊት ከሞቀ እንቅልፋቸው ሶስቴ ተቀስቅሰው፣አልጋው ረገበ አልረገበ በስጋት ተሰቅዘው አደሩና እንዳይነጋ የለ ነጋላቸው።ልጆቹ መታወቂያ ሊወስዱ ሲመጡ አብዬ አደፍርስ አልጋውን ሳላይ ገመድ ባንገቴ አሉ።አገላብጠው ካዩትና ከመረመሩት በኋላ
"እውነትም ላያስችል አይሰጥ!"ብለው አልጎመጎሙና ልጆቹን አሰናበቷቸው።በቀን ፈረቃ የሚሰራው ተተኪ ሰራተኛ እስኪመጣ ጠብቀው ስራ መልቀቃቸውን ነግሩትና ወደ ቤታቸው አዘገሙ።እመይቴ አማረች ወሬውን ቀድመው ከሂሩት ሰምተውት ኖሮ መሸት ሲል መጥተው የከረሰሰ ፊት ከከረሰሰ ሽሮ ጋር አቀረቡላቸው።
"አንቱ የሴት ገንዘብ ምን ምን ይላል?እስቲ ቀምሰው ይንገሩኝ "
ዘማርቆስ
@wogegnit
@wegoch
@wegoch
@wegoch
የዱር አበባ
የገጣሚ ቴዎድሮስ ካሳ የግጥም መፅሐፍ የፊታችን ቅዳሜ ሕዳር 28 ከ ቀኑ 11 ፡ 00 ጀምሮ መገናኛ በሚገኘው ሞሰብ የሙዚቃ ማዕከል ቅጥር ግቢ ውስጥ በድምቀት ይመረቃል ።
በእለቱ ሁላችሁም ተጋብዛችኋል።
@getem
ዕድሜዋ ወደ አርባዎቹ እየገሰገሰ ነው....በህይወት ውጣውረድ የዛለ ፊቷ አሁንም ድረስ ድንቡሽቡሽነቱን አላጣም። ዘውትር ለብሳት በምትዞረው አንድ ሺቲ ሙሉ ከተማውን ከጫፍ እስከ ጫፍ ታካልለዋለች። ካልነኳት ማትነካ ብቸኝነትንና ባይተዋርነትን የመረጠች ብቸኛ ነፍስ ናት። ፀጉሯን ማንጨብረር ወይም እንደ 90ዎቹ አፍሮ አርጎ ማቆየት ያስደስታታል። በዛ ድንቡሽቡሽ ገጿ እና ሺ ሀሳብ ቢያጠቃውም ፍንክች ባላለ ሰውነቷ እዚህም እዛም ትባዝናለች።
.
" ሰሚራ " ማህበረሰቡ እብድ የሚል ቅፅላ ሰጥቶ ቢያገላትም ፤ ለኔ ግን የተነጠቀችው ወጣትነት ፤ የተነጠቀችው ህልሟ ጎልቶ ይታየኛል። እደርስበታለሁ ካለችበት ፤ እኖረዋለሁ ካለችው ህይወት ተብትቦ ያደናቀፋት ማህበረሰብ ቀፅላ ሰጥቶ ቁስሏ ላይ ሌላ ቁስል የጨመረላት ምስኪን ነፍስ። የዛሬን አያርገውና አይምሮዋ ከመታወኩ በፊት እንደማንም ጤነኛና ለፍቶ አዳሪ ነበረች። በአንድ ወቅት ለምርመራ በሄድችበት ጊዜ የአባላዘር በሽታ እንዳለባት በሀኪሞች ይነገራታል። ከህይወት ጋ ግብግብ በገጠመችበት ወቅት ፤ አጋዥ ደጋፊ በሌላት ወቅት ይሄን መስማቱ ለእሷ የሞት ታህል ነበር።
.
ዐቅመ ቢስነቷ የእጇ ማጠር ፈውስን ነፍጎ በሽታዋን አበረታባት። ዕለት ተዕለት እየፀናባት ማህበረሰቡ የሚያስተውለው ደረጃ ሲደርስ ሁሉም አገለላት። ተፀይፎ በቃሽኝ ከማለት አልፎ ቅስምን የሚሰብሩ ቃላት እያቀበለ ጨርቋን አስጣላት። ከምላሳቸው ያወጧት ስንዝር ቃል ህልምና ውስጥኗን የቀረቻትን ጥቂት ተስፋ ይዞት ገደል ገባ። ጣት ጠቆሙባት መታመሟ ሳያንስ እብድ ነሽ ብለው የእብደት አክሊል አላበሷት....አሜን ብላ መኖር ቀጠለች።
.
ሳያት ታሳዝነኛለች ፤ እንዲህ ካረጋት ማህበረሰብ ጋር አሁንም ድረስ ተቻችላ ትኖራለች። ከሁሉ ከሁሉ ስታረገው ሳይ የሚያስደስተኝ አንድ ነገር አለ ። ብር እጇ ላይ ከሌለ መሃል አስፓልት ላይ ወጥታ መንገድ ትዘጋለች። ሚያውቋት ሹፌሮችም ባህሪዋን ስለሚያውቁ ገንዘብ ይሰጧታል።
.
ይሄን ስታረግ ሳይ ውስጤ ይረካል። ከመንገዷ ያደናቀፏትን ለደቂቃዎችም ቢሆን መንገዳቸውን አደናቅፋለች። ምትቀበለው ገንዘብ ለሞራሏ ካሳ ባይሆናትም ከኑሮ ወጪ ግን ይታደጋታል። ፖሊስ ቢመጣ ሰማይ ቢገለበጥ ከተቀመጠችበት ፍንክች አትልም። ታድያ በተቀበለችው ገንዘብ ቡና ልትጠጣ የጀበና ቡና ሻጮች ጋር ትሄዳለች። ማያውቋት ፈርተው የከለከሏት እንደው ትንሽ ግርግር መፍጠሯ አይቀርም። አምነው ለሰጧት ግን ሂሳበቸውን ሰጥታ ሲኒ በስርዓት መልሳ ካገኘች ጫት ካላገኘች ገረባ ሸክፋ ጥጓን ይዛ እየቃመች አልያም ተኝታ ቀኗን ታሳልፋለች።
.
ሚግባቧት ፍቅር ይሏታል ለሌቹ ደሞ በስሟ ይጠሯታል። ከወደደችህ በፍቅር ከጠላችህ ደሞ በስድብ አቀባበል ማድረጓ የተለመደ ነው። አንድ ጊዜ በመንገድ ሳልፍ ምን አበሳጭቷት እንደሆነ ባላውቅም ውሃ ደፍታ አጥምቃኛለች። ብቻ የአንደበታችን ኃይል እንደምናስበው ቀላል አይደለም። መጠገን ከሚችለው በላይ መስበር ይችልበታል። ይች ሴት ምን አልባትም አለውልሽ ሚላት ቢኖር መጨረሻዋ እንዲህ ባልሆነ ነበር። ለኛ ተራ እና ፌዝ መስለው ሚታዩን ቃላት በለሌላው ህይወት ላይ እንደ ደውል ቀን በቀን ያቃጭላሉ።
[ ጥሩቤል ]
@ebuhbhr
@wegoch
@wegoch
@paappii
ምን ማለት እንዳለበት ግራ ገብቶቷል። በሆነልኝ ያለው ነገር እጁ ስር መውደቁ ጨንቆቷል።ምንም ያህል ቢፈልገው፣ ምንም ያህል የእርሱ ይሆን ዘንድ ቢታትርም፤ የድካሙ ውጤት አሁን መከሰቱ ከደስታው በላይ ፀፀትን፣ ከፌሽታ በላይ ሀሳብን ወልዶለታል። አይ ጊዜ፣ ወይ ስሜት ።
ቀኗ ለሷ ልዩ ነው። ጎህ ሲቀድ የውበቷን ልክ ለአፍቃሪዎቿ ልታስኮመኩም የቆመችው ውብ ፀሐይ ለቀኗ ማማር አንዳችስ እንኳን አስተዋጽኦ የላትም፤ እንደው የምሽቱ ውበት፡ ጨረቃና ኮከቦች ለሳቋ ምንጭ ሆኑ እንጂ። የሸበበው ልቧ የአንዲት አፍላ ኮረዳ መልክ የተቀዳጀላት ቀኑን በቀኝ እውለኝ በሚል ተስፋ አልያም ያስዋቧት ጌጣጌጦች አይደሉም። የቀኗ ማማር ዋናው ምክንያት፡ ስሜቷ፤ ያ ያሻችው ልቧን ያድነው ዘንድ የተማፀነችው እውን መሆኑ እንጂ።የቀኗ ማማር ሚስጥር የፈለገችው፡ እንዲሆንላት አብልጣ የወደደችው በመሳካቱ ነው ። ወይ ስሜ....ት!።
አንድ ቀን! ሁለት አይነት ስሜት፤ ለአንዱ ፌሽታ ለአንዱ ደግሞ ዱብዳ። ከፈካው ቀኗ በፊት ባለው ምሽት ያልወጣላትን ፍቅሯን አግኝቷው ነበር። ህይወት አንድ ዩኒቨርስቲ ነው ያገናኘቻቸው። እጅግ ሲበዛ ጨዋታ አዋቂ ነው። እሱ ካለ ዝምታ አይታሰብም። እርሱን ያገኘች ነፍስ ሳትፈልግ ከንፈሯን ትገልጥለታለች፤ በቀልዶቹ ድዶች ሁላ ይስቁለታል። ከሱ ጋር መዋል ለጤና ጥቅም አለው ሳይባል ሚቀርስ አይመስልም። ማንም ሴት ቀርቧው ዳግመኛ ባላየሁት ምትል አይነት ወንድ አይደለም። ቁመኗው ከፀጉሩ መሸሽ ጋር ተደምሮ ከጨዋታው ይበልጡኑ አስውበውታል። የአንዲት ምሽት አጋጣሚ ቢያገናኛትም በቀልዶቹ፣ በማያባራ ወሬው ጎርፍ መወሰዷን የአይኖቿ መመሰጥ ያሳብቁባታል። የጠይም ቆንጆ ናት። ስለ ጠይም ቁንጅና መዝገበ ቃሉ ፍቺውን እሷን እዩልኝ ብሏል። ከሰው ጋር ቶሎ የመግባባትን ተስጥዖ ፈጣሪ አዳልቶ ለሷ የሰጣት ነው ምትመስለው። ጨዋታ ይገባታል፤ የቀልዶች ቅመም እሷ ናት። ጥርሷ ሁሌ ስራ እንደበዛበት ነው። ከሷ አጠገብ ዲዳ ሁላ ያወራል። መተከዝህን መከፋትህን ታስረሳኻለች።
ለወደፊት ህይወታቸው መሸጋገሪያ ትሆን ዘንድ በሚኳትኑባት ዩኒቨርስቲ ባልታሰበች አጋጣሚ ነው በጓደኞቻቸው አማካኝነት የተዋወቁት። እሷም እሱም ለመግባባት የማቱሳላ ያህል እድሜ አላስፈለጋቸውም። ምሽቱን ጨዋታና ፌሽታ ከበበው። ከዛ በኋላ ነው የነሱ ፍቅር ጉዞ ዕለት ተ ዕለት እያደገ የመጣው። መገናኘት፡ ማምሸት፡ ማውራት፡ መጫወት፤ ደግሞ መገናኘት፡ መሯሯጥ፡ መዝፈን፡ መዝለል፤ ድጋሚ መገናኘት፡ ማውራት፡ ማውራት፡ ድጋሚም ማውራት፡ በጣም ማውራት: ይበልጡኑ ማውራት ስራቸው አረጉት። ዕለት ተ ዕለት ኮከብ ከመቆጠራቸው የተነሳ ኮከቦች ከነሱ መሸሹን ከጀመሩ ሰነባብተዋል። ቀናት በነጎዱ ቁጥር ፍቅራቸው ይጨምር ጀመር። ጊዜም ከነሱ ጋር አብሮ መጓዙን ተያይዞታል።
ያቺ ምሽት ፍቅሯን መልሳ ያገኘችበት ቀን። በፍቅር መሀል በተፈጠረ ግጭት ከተጣሉ ሰነባብተዋል። እሱም ከትምህርት በተጨማሪ ለነገው ህይወት ዛሬ ላይ መሰነቁን አልዘነጋውም። በጓደኞቻቸው መሰባሰብ የተራራቁ ልብን ስጋ ያገናኛቸው ጀምሯል። እንደመጀመሪያው የግጭት ሰሞናት መዘጋጋትን ትተዋል። ፍቅረኛ የሚትባል ቃል በሁለቱ መሀል ባትኖርም የጎሪጥ መተያየቱን ትተው ማውራት ከጀምሩ ሰነበቱ። በዛ አጋጣሚ ውስጥ ነው የሷን ፈገግታ፡ እየወደደችው የራቀችውን፤ ባለመግባባት ያጣችውን ፍቅሯን መልሳ ያገኘችው። በዛ አጋጣሚ ነበር ቃላቷ ፍቅርን ዘርተው ያናግሩት የጀመሩት። ያቺ ቀን ናት ፍቅሯ እንደ ገደል-ማሚቱ ለልቡ ያስተጋቡለት። መራራቅ፡ መጣላት፡ መኮራረፍ፡ ፍቅሯን እንዳላሳጣው ያቺ ቀን ገልጣለታለች። የትላንቱ እሱነት ዛሬ ላይ አይታይበትም። ያቺ ምሽት ፍቅርን መለሰች። ፍቅረኛ በሚባል አጥር ድጋሚ አጠረቻቸው።
ምን ማለት እንዳለበት ግራ ገብቶቷል። በሆነልኝ ያለው ነገር እጁ ስር መውደቁ ጨንቆቷል። ምድር ብትውጠው ደስ ይለዋል። በተጣሉበት ጊዜ የጀመረው የውጭ ትምህርት እድል ተሳክቶለታል። ምንም ያህል ቢፈልገው፣ ምንም ያህል የእርሱ ይሆን ዘንድ ቢታትርም፤ የድካሙ ውጤት አሁን መከሰቱ ከደስታው በላይ ፀፀትን፣ ከፌሽታ በላይ ሀሳብን ወልዶለታል። እንደትላንት አብሯት ሊቀጥል፤ በፍቅር አብሯት ሊዘልቅ የወሰነ ሰው ዛሬ ላይ አብሯት የማይቀጥልበት ሁኔታ ሲፈጠር መግቢያ መውጫው ጠፍቶቷል። ስሜቷ፡ ፍቅሯ ላይ ድጋሚ ሊጫወትባት መሆኑ ተሰማው። አሳዘነችው። ትላንት አብረን እንቀጥል ሲላት የተሰማትን ደስታ ሊነጥቃት መሆኑን ሲያስብ ዘገነነው። ወይ ጊዜ እድልን አትሰጥ ነገር፤ ህይወት ትላንቱን እንዲያርም አንድ እድል ብትሰጠው ምንኛ ደስ ባለው ነበር። "አብረን እንቀጥላለን" ብሎ የሰጣት ተስፋ ፊቷን እንዳበራላት ያውቀዋል። መሄዱ የማይቀር ነገር ነው። ነገር ግን እሷን ምን ያርግ? ምን ይበላት?። ትላንትናውን ጠላው። ይንገራት ወይስ ለመሄድ የቀሩትን ጥቂት ቀናት ፍቅረኛዋ ሆኖ እንደሚቀጥል ያስመስል? ጨነቀው! አዘነላት፤ አሁኑኑ ቢነግራት ደስታዋን ሚነጥቃት መሰለው። በየቀናቶቹ ለመንገር ይወስንና ባገኛት፡ ባወጋት ቁጥር አብረው በሚያሳልፉት ጊዜ ምኖራትን ደስታና ፈገግታዋን ባየ ቁጥር ፤ አስችሎት ቢነግራት ያ...ን ደማቅ ፊቷን ሚነፍጋት መስሎ ታየው። "ምነግርሽ ነገር አለ" የሁል ቀኑ ተግባር፡ "ሌላ ቀን" የሀሳቡ መቋጫ ሆኑት። ነግሯት ደስታዋን፡ ያከመውን ልቧን ድጋሚ ሲጎዳው ምን ይሰማት ይሆን? ህይወት በራሷ መንገድ አገናኝታ በራሷ መንገድ ስታራርቃቸው ምን ትል ይሆን? ብዙ ቢጨነቅላትም እንዳትጎዳ ቢሸሽጋትም የመሄጃው ጊዜ እሱ እስኪወስን እየጠበቀው አልነበረው። ጊዜና ስሜት! መራቅና ፍቅር! አቤት ህይወት... እንደፈለገች ምታሾልበት!
ሰማዩ ከሱ ጋር ያዘነ ይመስል ማልቀሱን ተያይዟል። ሊነግራት ወስኗል። ሊያሳውቃት፡ እንደሚያማት፡ ለመቀበል እንደሚከብዳት እያወቀ ሊነግራት ወሰኗል። ምንም አማራጭ የለውም። በዝምታ መቆየቱ ይበልጡኑ ኋላ እንደሚጎዳት ተሰማው። በአካል አግኝቶ ሊነግራት ወሰነ። ሊያገኛት ደወለላት "Hello...."።
By 乃丨丂尺卂ㄒ
@wegoch
@wegoch
@paappii
እህቴ ነበር ያሳደገችኝ:-
አራት ወይ አምስት አመት እያለሁ ነበር ወላጆቻችን ወደ ሞት የሄዱብን ። ሁለት ብቻ ነበር የወለዱት : እኔን እና እህቴን ። ስምንት አመት ትበልጠኝ ነበር ። መቼ ወደ አባትነት ፣ መቼ ወደ እናትነት እንደተቀየረች አላውቅም ።
ቤታችን ውስጥ አባትና እናት የሚወጣውን ሃላፊነት ተሸከመች ። ሸክሙ አላስጠናትም መሰለኝ ትምህርት አልገፋችም። አስረኛ ላይ የሙያ ውጤት መቶላት ነበር፤ እሱንም ተወችው ።
አልምልም : ከማልኩ ኤልዱ ትሙት እላለሁ በቃ ። ምድር ላይ ሞት መጥቶ ቻው ማለት የምትፈልገው ሰው ብባል፣ ዘመድ ጥራ ብባል ፣ አንደኛ ማን ያስብልሃል ብባል ፣ የማን ወዝ እና ህልም አልፎብሃል ብባል መልሴ ኤልዳና የሚል ብቻ ነው ።
ተሰብስበን ህልም ስንናገር ኤልዳና ህልሟ እኔ ነበርኩ ። እንደዚህ ሰው ይወደዳል እንዴ? እንደዚህ በፍቃድ ህልም ይሰዋል ? የሆነ ቀን ከስራ ስመጣ ኤልዳ ታማ ጠበቀችኝ ። ክሊኒክ ወሰድኳት ቀላል አይደለም ብለው ሪፈር ላኩን ።
ፊቷ ችፍፍፍ ፣ ቁስልስል አለ ። ቀኝ እግሯ እምቢ አላራምድ አለ ፣ ምግብ አልበላ አላት ። ብዙ ቦታ ሄድን መፍትሄ አጣን ።
ኢ- አማኝ ነበርኩ ፤ እንዲ አደረክብኝ ብዬ የምጠይቀው አካል፣ እንዲ አድርግልኝ ብዬ የምለምነው አካል የለም ። ነፍስ ካወኩ እንዲ ሀዘን ተጣብቶኝ አያውቅም ። የመኖር ፍላጎት እና ህልሜ ከሰመ። ህመሟን አለምደው አልኩ ። ሃኪሞች ተስፋ የላችሁም አሉን ።
የሆነ ቀን አስራ አንድ ሰዓት ለሊት ቀስቅሳኝ
"በዓታ ማርያም ሶስት ቀን ፀበል ተጠመቂ ትድኛለሽ ተባልኩ" አለችኝ ። ማመን የማይደክማት ልጅ ፤ መሞኘት የማይሰለቻት ልጅ ።
"እሺ እንሂድ" አልኳት ።
አማራጭ የሌለው ሰው ምንም አይፈላሰፍም። እንኳን ቤተክርስቲያን ስምጥ ሸለቆ እሄዳለሁ ። በርግጥ እኔ ከ 'Bible' የ Sigmund Freud - 'The Future of an Illusion' የተሻለ ያሳምነኛል።
ግን፤ ኤልዱ እድናለሁ ካለች የት አልሄድም ??
ሄድኩ : ተጠበለች ወደቤት መጣን ። እሷ በህልሟ፣ እሷ በበኣታ ፣እሷ በፀበል ያላት እምነት ትልቅ ነበር እና ውጤት ጠበቀች በርግጥ እኔ የምጠብቀው ነገር የለም ።
በነጋታው ጠዋት ፊቷ ለውጥ ያለው መስሎኝ ነበር እሷ አረጋገጠችልኝ ። በሁለተኛው ቀን ሄድን "እግሬ ቀለለኝ" እያለች ነበር ። የዛ ቀን በነጋታው "እግሬ ሰራ " አለች ።
የሆነ ነገር ማለት ፈልጌ ነበር ደስታ፣ እምባ አላናግር አለኝ እና ዝም አልኩ። ሶስተኛ ቀን ተጠመቀች ፊቷ፣ እግሯ ፣የምግብ ፍላጎቷ እንደነበረ ሆነ ።
ሶስተኛ ቀን እሷ ተጠምቃ ስትጨርስ "ወደቤት እንሂድ ወይ?" አለችኝ።
"እኔ ልጠመቅ እና እንሄዳለን" አልኳት። ስትድን ደስ ያላትን ያህል ደስ አላት። ሆድ ብሶኝ ነበር ፣ደስ ብሎኝ ነበር ፣ ማመን አቅቶኝ ነበር። እያለቀስኩ እያመሰገንኩ እየተደሰትኩ ተጠመኩ አመንኩ ።
ሃሌ ሉያ ❤
By Adhanom Mitiku
@wegoch
@wegoch
@paappii
ሥዕል ማሳል ለምትፈልጉ በሙሉ
በ +251984740577
ወይም @gebriel_19 ላይ ፎቶ በመላክ በ ተመጣጣኝ ዋጋ ማዘዝ ይችላሉ!
#ሥዕል_ብቻ
@seiloch
@seiloch
[ ድንግል ደሟን መልስ ! ]
ሰላም ሉሌ ፤ እስኪ ልተንፍስ ። ባህር ዳር ዩኒቨርስቲ ፓሊ ግቢ ነው ፤ አባይ ማዶ የሚባል ሰፈር አባይ ድልድይ ስር ከወንዙ አጠገብ ጫት መቃሚያ ቤት አለ ። ያው ፥ ልንቅም ከዶርም ጓደኞቼ ጋር እንሄዳለን።
ከአዲስ አበባ የመጣ ቆንጅዬና ተግባቢ የሆነ የዶርም አባላችን አንድ የአባይ ዳር የጠንቋይ ልጅ ይተዋወቃል። ልጅቷ ያኔ ገና ለአቅመ ሄዋን አልደረሰችም ፥ ብቻ ተግባቡ፡፡ ሌላ አብሮን ዶርም ሜታችን የሆነ የባህር ዳር ልጅ ደግሞ ጓደኛችንን "እቺ የጠንቋይ ልጅ ድንግል ከሆነች ድንግልዋን ብትወስድ እና ኋላ ብተዋት ደም መልስ ትባላለህ። አርፈህ ተቀመጥ!'' ይለዋል።
ጓደኛችን ግን ብሶ ተገኘ ፤ ከልጅቷ ጋር ይበልጥ እየተግባቡ መጡ፡፡ አብረው ለመተኛት ተስማሙ ግን ልጅቷ እኔ ሆቴል አላድርም ''አባይ ዳር ጎጆ" ከሆነ ብቻ ነው እሺ የምለው አለች። አባይ ዳር ወንዝ ማዶ ላይ ሌሊት ሌሊት ለጥንቁልና ስራ የሚውሉ ጎጆዎች አሉ ። እዛ ማለቷ ነው፡፡
የሆነ ቀን ላይ ታዲያ ተስማምቶ ፥ እዛው ድንግልናዋን ወሰደ ። ከተወሰኑ ወራት በኋላ ግን ልጁ ግቢ ውስጥ ሌላ ቺክ ጠበሰ ። የአባይ ዳሯን ልጅ ቀስ እያለ ተዋት ፡፡ እያደር ፥ አባይ ማዶም ጫት ለመቃም መሄድ አቆመ ። አጥብቃ ስትደውል ፥ ስልኳንም ከነአካቴው ማንሳት ተወ ።
እናልህ ልሌ ፤ አንድ ቅዳሜ እኔና ያ ሌላኛው የባህር ዳር ልጅ ልንቅም ስንሄድ በእኛ በኩል አድርሱለት ብላ መልእክት ላከችብን...
''በቃ ፥ ከተወኝ ደሜን ይመልስ ! ካለበለዚያ እወስደዋለሁ"።
መልእክቱን ነገርነው። "የጠንቋይ ልጅ ነኝ ብላ ታስፈራራኛለች እንዴ ? ስለምን ደም መመለስ ነው የምታወራው? ምንም አታመጣም'' ብሎ ዝም አለ።
ከጥቂት ቀናት በኋላ ከልጁ ጋር አብረን ሁነን አቅራቢያችን ወደ ሚገኘው አቡሄ ቤ/ን እየሄድን ሳለ አንድ ነገር ገጠመን ። ጥቁር በጥቁር የለበሰ ፣ ራሱን ደማቅ ቀይ ጨርቅ የጠመጠመና ፣ በእጁ ቀይ ጨሌና የሚጨስ ሰንደል የያዘ ከሰል የመሰለ አይኑ የሚያስፈራ ሰው ባዶ እግሩን ፊት ለፊታችን መጥቶ መንገዳችንን ዘጋ ።
በኋላ ጓደኛዬን እጁን ግጥም አድርጎ "ነገ ማታ 1 ሰዓት ላይ አባይ ድልድይ ስር እንድትመጣ ጌቶች ልከውብሃል ። ነገ ሌሊት 9 ሰዓት ላይ ደሟን ትመልሳለህ። ደሟን መልስ ካለበለዚያ እወስድሃለሁ" ብለዋል ! ብሎ በእጁ የያዘውን ሰንደል ወደ ጓደኛዬ አፍንጫ በግድ አስጠግቶ አስሸተተው፡፡
እኔና ጓደኛዬም በሆነው ነገር ተደናግጠን ቤተክርስቲያን መሄዱን ትተነው ወደ ግቢ ተመልሰን ለባህር ዳሩ ዶርም ሜታችን ነገርነው። ''ደም መልስ እያሉኝ የምን ደም ነው የምመልሰው? ምን አድርግ ነው የሚሉኝ እነዚህ ሰዎች" አለው?
ልጁም " ከዚህ በፊት ነግሬሃለሁ እኮ ! ሌሊት በተነገረህ ሰዓት ብልትህን በምላጭ ቆርጠህ ሲደማ ደሙን በቡና አተላ ትለውስና ሽቶ ረጭተህ ወደ አባይ ወንዝ ትጨምርዋለህ። ያኔ ድንግልናዋን ስትወስድ የፈሰሰው ደም እንደመለስክ ይቆጠራል ፤ ከዚህ በላይ ግን ዝርዝሩን አልነግርህም" ብሎ ለኔም ለእሱም ከዚህ በፊት የነገረንን ደገመለት።
ጓደኛችንም "ታመራለህ እንዴ? ያኔም ስትነግረን ልታስፈራራኝ ሙድ እየያዝክብኝ መስሎኝ ነው፡፡ አብጃለሁ እንዴ ይሄን የማረገው የሚያመጡትን አያለሁ ብሎ'' ስቆ ዝም አለ። ሲቆይ ፥ ተረሳ ነገር ።
ከሳምንታት በኋላ Final Exam ጨርሰን ጣና ያሉ ደሴቶችን እንጎብኝ ብለን አራት የዶርም አባላት ሁነን የሞተር ጀልባ ተከራየን ። በሀይቁ እየሄድን በአራቱም አቅጣጫ ከውሃ ውጭ ምንም የማይታይበት ቦታ ስንደርስ ...
- "አንተ ሳሚ ባለፈው መንገድ የዘጋብን ጥቁር ሰውዬ የያዘው ሰንደል አይነት አይሸትህም?'' አለኝ።
- "ኧረ እኔ አይሸተኝም" አልኩት። "እንዴ ሌሎቻችሁስ የሰንደል ጭስ አይሸታችሁም?'' ሲል ሁለቱም ኧረ ምንም አይሸተንም አሉ፡፡
ጀልባዋን የሚነዳት ልጅ ፥ ኧረ ሰንደል ሀይቅ ላይ ሲሸት ጥሩ አይደለም "በስማም በል!' አለው። ልጁ እየሳቀ የሚገርም ነው ለኔ እንዲያውም ሽታው እየጨመረ መጣ አለን ። በውሀው ለመፍታታት ፥ ከአጠገባችን ብድግ ብሎ ወደ ጀልባዋ ጫፍ ላይ ሂዶ ሀይቁን በእጁ ጨለፍ ጨለፍ እያደረገው ሳለ ፤ አስደንጋጭ ነገር ተከሰተ ።
የሆነ እጅ የጓዳችንን እጅ ስቦ ፥ ወደ ሀይቁ ከተተው ፡፡ እኔ ሁሉንም አይቻለሁ ፤ ፊት ለፊቱ ነበርኩ ። ልጁን እንቅ ያደረገውን እጅ በሚገባ እኔና አንዱ ጓደኛዬ ተመልክተንዋል። ሌላኛው ጓደኛችን ከጀልባ ነጂው ጋር እያወራ ስለነበረ አላስተዋለውም።
የወንድ እጅ ፈፅሞ አይደለም። ፍም የመሰለ ቀይ የሴት እጅ! ሁላችንም በድንጋጤ ጮህን ሁላችንም እያየነው አንገቱ ብቻ እየታየ ምንም መጮህ ወይንም መናገር ሳይችል ለተወሰኑ ሰከንዶች ወደ ኋላ ከተጓዘ በኋላ አንገቱ ወደ ሀይቁ ጠለቀ። ምንም አይነት መንፈራገጥ አላሳየም። በቃ አይኖቹ እንደፈጠጡ፣ ምንም ድምፅ ማሰማት ሳይችል ልክ ከባድ እቃ ባህር ላይ ተወርውሮ ትንሽ ተንሳፎ ወዲያው ስምጥ እንደሚለው ወደ ውስጥ ቡልቅ ብሎ ጠለቀ።
የጓደኛዬ የፈጠጡ አይኖችና ሁኔታው በህልሜ እየመጣ እየቃዠሁ ለብዙ ጊዜ ተቸግሬያለሁ። ሳይካትሪስት ጋር ሂጄ እስከ መታከም ደርሼ ተገቢውን የህክምና ክትትል አድርጌ አሁን መለስ ያልኹ ቢሆንም ፥ ከዛ በኋላ እስከዛሬ ድረስ ውሃ እፈራለሁ።
ሐይቅም ሆነ ወንዝ ላይ በምንም አይነት ሁኔታ ለመጓዝ ድፍረት የለኝም። ሉሌ ፤ ለስብሰባ የምሄድባቸው የሆቴሌ ገንዳዎች ውስጥ እንኳን ለመዋኘት ድፍረቱን አጣለሁ ፥ አለ አይደል በዛው የምቀር ይመስለኛል። ሰንደል የሚሉት ነገርም ጨርሶ ጠላሁ ፥ ሲሸተኝ ሁሉ ያመኛል። ምን ልልህ ነው ፤ አንዳንድ ጊዜ በህይወታችን ውስጥ የሚፈጠሩ አጋጣሚዎች ስነ-ልቦናችንን ምንም ባልጠበቅነው መልኩ ይቀይሩታል ፡፡
By leul Zewelde (Inbox)
@wegoch
@wegoch
@paappii
የካቲት ወርሀ-ገብረ-ክርስቶስ ;
ቅዳሜ የካቲት 29 ቀን 2017 ዓ/ም ከቀኑ 8:30 ሰአት በገብረ ክርስቶስ ሙዚየም 6 ኪሎ ፧ አመታዊው አለማቀፍ የገብረክርስቶስ ቀን በስነ ግጥምና ስነ ጥበብ ደምቆ ይከበራል። ገብረክርስቶስንና ድንቅ ስራዎቹን የምትወዱ ሁሉ ተጋብዛችሁዋል። ፕሮግራሙ በቀጥታ ስርጭት ይተላለፋል።
ምንጭ
አርቲስት በቀለ መኮንን
@Seiloch
ሲራክን አገባለው ብዬ ማልቀስ ከጀመርኩ ወዲያ እማዬም አባዬም ቤተሰቡም ጎረቤቱም ሁሉ እኔን እንደ ሞኝ ነው የሚያዩኝ ። እማዬም ሞኝነቴን ከርዝመቴ ጋር እያገናኘች " ከኩዮቿ ስትረዝም ነውኮ ጉድ የመጣው ድሮም ረጅም ሰው ሞኝ ነው " ትላለች በርግጥ ሞኝ ምን ማለት እንደሆነም መጀመሪያ አካባቢ አላውቅም ነበር ቡሀላ የሆነቀን አክስቴ የኔን ካላገባው ወሬ ሰምታ
"አንቺ ሞኝ ጅላንፎ ጅል ሲራክኮ ቢወልድ ያደርስሻል በዛ ላይ እሱቴ ምን በወጣው ያቺን መልአክ መሳይ እጮኛውን ትቶ ሆሆሆሆ እኩያሽን ፈልጊ ምን ውርንጭላ ናት ይቺ" ብላኝ ነው ሞኝነት የጅልነት ተመሳሳይ ፍቺ መሆኑን የደረስኩበት ። አክስቴ ያን ቀን ስለ ሲራክ እጮኛ መልኣክ መምሰል ስትናገር መልአኮች ምን ይምሰሉ ምን ሳላውቅ እርግፍ አረገው ነው የደበሩኝ (ይቅርታ እንግዲ እግዚአብሔር ምን ላርግ በሲራክ መጡብኛ) ሴጣንንም ብትመስልኮ ያቺ ሚያገባት ሴትዮ ሴጣንን እጠላ ነበር ማን መልኣክ ምሰይ አላት ብቻ ሲራክ መልአክ ምትመስል እጮኛ አለችው ። ግን እጮኛ ምንድን ነው ሚያረግለት? እጮኛ ማለት ሚገባ ሰው መሆኑን ከአክስቴ አወራር ገብቶኛል ሲራክ ግን እጮኛ ሲያስጠላበት !!
የዛን እለት እንባዬን እያዘራው ሄድኩ እነ ሲራክ ቤት ቀጥ ብዬ ቤታቸው ስገባ የሲራክ እናት ዳንቴላቸውን እየሰሩ አገኘዋቸው ሳግ በተናነቀው ድምፄ
"እማማ ሲራክስ" እንባዬ በጉንጮቼ ያለማቋረጥ ይወርዳል።
" እንዴ በሞትኩት እመብርሀን ድረሽ ምንድን ነው ሚጡሻ ምን ሆነሽ ነው ምታለቅሽው ሲራክ ምን አርጎሽ ነው ልጄ" አሉኝ ዳንቴላቸውን ጥለው ወደኔ እየመጡ ።
"ሲራክ ሌላ ሚያገባት እጮጬኛም አለችው ደሞ ደሞ መልኣክ ነው የምትመስለው ብላኛለች አክስቴ ደሞ ሲራክ እኔን አያገባኝማ " ብዬ ለቅሶዬን አቀለጥኩት
" ምን ጉድ ነው ዘንድሮ ኧረ ተይ ሚጡ ተይ (ለኔ)
ምነው አፌን ቢቆርጠው እንደው ለሲራኬ ነው ምድርሽ ያልኳት ቀን (ለራሳቸው)" እንባዬን እና ንፍጤን በለበሱት ነጠላ እየጠረጉ
ሲራክን እንደማገባ እንጂ ማን አንደዛ ብሎ እንደነገረኝ ረስቼው ነበር አሁን እሳቸው እንዳሉኝ ራሳቸው አስታወሱኝ ። አዎ እሳቸው ናቸው እነሱ ደጃፍ ላይ ባልና ሚስት እቃቃ እየተጫወትን እኔና ስምረት እኔ ነኝ ሚስት ምሆነው ተባብለን ስንጣላ የገላገሉ መስሏቸው እኔን ረጅምም ስለሆንኩ ባል ከሚሆነው ከሄኖክ ጋር ስለማልመጣጠን ለዛሬ እኔ ሚዜ እንድሆን ሲነግሩኝ " እኽ እና ሁሉም ሚጫወቱት ወንዶችኮ አጭር ናቸው መቼም ላላገባ ነው እንዴ " ብዬ ለንቦጬን ስጥል(እማዬ ናት ሳኮርፍ ለንቦጭሽን አትጣዪ ምትለውእንደውነታው ከሆነ ግን ምንም አልጣልኩምኮ ሲጀመር ለንቦጭ ሚባልም እቃ የለኝም ) ብቻ እሱን ነገር ስጥል ራሳቸው ናቸው በቃ አንቺ ሲራክን ታገቢያለሽ ብለው የነገሩኝ ። ይኸው አሁንም አክስቴ ያለችው ውሸት መሆኑን እንዲያረጋግጡልኝ ጎናቸው አለቅሳለው
" ደሞ ደሞ እኔ ሚካኤን አልመስልማ እማማ "በእንባ በታመቁ አይኖቼ እያየዋቸው መልሳቸውን እጠብቃለው ከማውቃቸው መልኣክት ሚካኤልን ለምን እንደመረጥኩ ግን እንጃ
"ማለት ሚካኤልን ደሞ እዚ ምን አመጣው"
"ሲራክ ሚፈልገው መልኣክ ማግባት አይደል" መሀል መሀል ላይ ሳግ እያቋረጠኝ
" ቅዱስ ሚካኤል ድረስ ምን ስትይ አመጣሽው አንቺ ልጄን ልታስቀፅፊ ነው እንዲ ምትይ አበስኩ ገበርኩት እንደው እመብርሀን ይቅር ትበልሽ ሆሆ "
"ታዲያ እጫጩ ኛውስ "
ሳያስቡት ሳቃቸው እያመለጣቸው " እጮኛ ማለት እንኳን ማትችዪ ድንቢጥ እንደው ምን ብለሽ ነው ይሄን ሲራክን ምታገቢው በይ "
" ችግር የለውምኮ እማማ እስኪያገባኝ እለማመዳለው " ለቅሶዬን አቁሜ
" ሚጣሹ እንግዲያውስ እረፊው ሲራክ አያገባሽም !!"
"ለምን?" እየተኮሳተርኩ
"ማግባት ምን እንደሆነ ግን ታውቂያለሽ " አይኖቼን እያዩ
ደነገጥኩ ግን ምንድን ነው መጋባት ወዲያው አይምሮዬ ላይ የመጡት ጓደኞቼ የቃቃ ባልና ሚስቱ ነበሩ ቀልጠፍ ብዬ
"እንደ ሄኖክና ስምረት መሆን ነዋ"
"እኮ በቃ ሲራክ ደሞ ካንቺጋ እንደዛ አይሆንም"
"ኧህ እኮ ለምን ?"
" አንቺ ሄኖክን ያላገባሽው ከሱ ስለምትረዝሚ አይደል ሚጢሹ ሲራክም ቁመት ስለምበልጣት አላገባትም ብሏል እንግዲ እረፊው " አሳመኑኝ እውነታቸው ትንሿ ጭንቅላቴ ውስጥ ነብስ ዘራች
"እንጂ መልኣክ ስላለው አደለማ ?" የመላእክ መምሰሉ ጉዳይ እየከነከነኝ
" ኧረ እቴ ረዥም እኩያውን ሊያገባ ፈልጎ ነው አንቺም የቁመት እኩያ ስታገኚ ታገቢያለሽ እሺ ሚጢሹ" አመንኩበት ።
በቃ እንደውም ሲራክን አላገባም!
by kalkidan solomon
@wegoch
@wegoch
@paappii
‹‹ሥራ ካለው ቦርጭ አለው››
"ላግባ እንዴ ለምትል ላጤ ሴት ካገባችና ( እስካሁን) ደስተኛ በሆነ ትዳር ውስጥ ከምትገኝ ባለትዳር ሴት የቀረበ ምክረ ሃሳብ "
(ርእስ ነው)
++++++
እንግዲህ ካገባሁ ሁለት አስርት ዓመታት ልደፍን ትንሽ ቀረኝ።
ወቅቱ የሰርግ ነው፣ እኔም ቢከርምም ሙሽርነቴ በጥር ነበርና፣
እነሆ ስለትዳር ሃቅ ሃቁን መስማትን ለምትፈልጉ እንስቶች
እቅጭ እቅጩን ፣ ነጭ ነጩን
ሳላሞካሽ፣ ሳልቀባባ፣
እንደሚከተለው እመክራለሁ።
ቅድመ-ጋብቻ
------
ምርጫ ተትረፍርፎልሽ "ማንን ላግባ" በሚል የግርታ ጉም ተጋርደሽ ከሆነ
ከዚህ በታች ያለው ሊጠቅምሽ ይችላልና አንብቢው፡፡
እቱ ገላ!
ከሁሉ በፊት ይህንን እወቂ!
አንድ)
ለትዳር ብቁ የሆነ ወንድ…
ስራ ካለው ቦርጭ አለው።
ብር ካለው መላጣ ነው።
ታታሪና ቤቴ ቤቴ ባይ አባወራ ሰላላ እግሮችና ነጋሪት ሆድ እንጂ ጡንቻና ሲክስ ፓክ ይለውም።
አብላጫው ወንድ ገንዘብ በበሩ ሲገባ ፀጉሩ በመስኮት ይወጣል።
ፀጉሩ ያላፈገፈገ፣ ባለሞዴል አቋም እና ሃላፊነት የሚሰማው ወንድ በአንድነት ባል ሆነው ሲመጡ ካየን ቆይተናል።
ስለዚህ ምርጫሽ ላይ ተጠንቀቂ።
‹‹ሲክስ አብ›› አይተሽ፣ በባትና ደረቱ ተማርከሽ ስታለከልኪ፣ አጇኳሚው ላይ እንዳትወድቂ።
ሁለት )
አበባ እየገዛ እሾህ ከሚሆንብሽ፣ ቫኬሽን እያዞረሽ ዓይኑ ሌላ ከሚቀላውጥ ወንድ ይልቅ ሮማንቲክ ባይሆንም፣ ገና እምቦቃቅላ ሳለሽ የትራስ ጨርቅሽን የቬሎ የራስ ልብስ አስመስለሽ ያገባሽው የእቃቃ ባልሽ አይነት ባይሆንም ፣
( እንደ አቅሙ) የሚያስፈልግሽን ነገር ሳትጠይቂው የሚያደርግልሽን ሰው ባል ካደረግሽ መለስተኛ ገነት ገባሽ። ይሄን ስልሽ አበባ ሰጥቶ ማር፣ ቫኬሽን አዙሮ ታማኝ የሆነ ወንድ የለም ማለቴ አይደለም፡፡ ግን ብዙ አይደሉም፡፡ ካሉም አግብተዋል፡፡
ስለዚህ….አብዛኛው አይነት ገጥሞሽ በብልጥልጥና ጊዜያዊ ብልጭልጭ ነገር ተታለሽ ይህን ከሳትሽ ዘላቂ ሲኦል ወረድሽ።
እሺ…መምረጡንስ መረጥኩ…ግን ለመሆኑ ትዳር ግን እንዴት ነው? ካልሽ ደግሞ የሚከተለውን ተመልከች።
አንድ)
ትዳር ነጋ ጠባ የምትሳሳሚበትና ፍትፍት እየተጎራረስሽ" ፍቅርዬ ወዬ ወዬ" የምትባባይበት ሮማንቲክ ኮሜዲ አይደለም።
ዘጠና በመቶው ሎጅስቲክ ፣ አሰልቺ የቀን ተቀን ኑሮን መግፊያ መስተጋብር፣ ደሞዝ አልባ ስራ ነው።
እውነቱን ፍርጥርጥርጥ አድርጌ ልንገርሽ?
የት ነህ)የት ደረስክ) ልጆቹ ምግብ በሉ?) አምፖሉን መግዛት እንዳትረሳ) ዳይፐር ይዘህ ና) እናትህ ዛሬም ይመጣሉ) ቀዩን ሸሚዜንን የት ከተትሽው) እራት ዛሬም ምስር ነው) ሁሌ እርጥብ እየበላሽ እንዴት ልትከሺ ነው)
ዓይነት ነገር ይበዛዋል።
ከዚያ ግን አልፎ አልፎ በፊት፣ ገና አፍላ ፍቅር ላይ ሳላችሁ እንደሚያደርገው አየት፣እቅፍ፣ ሳም፣ ውድድ ሲያደርግሽ ነፍስ ትዘሪያለሽ።
የሆነ ሰውዬ ሚስትና የሆኑ ልጆች እናት ከመሆንሽ በፊት ማን እንደነበርሽ ትዝ ይልሻል።
ሴክሲ ሴክሲ ያጫውትሻል።
እንኳን አገባሁ ትያለሽ።
ወዲያው ግን በፍቅር ድግስ ልባችሁ ጠፍቶ ደክማችሁ በተንጋለላችሁበት፣
"አከራያችን ደጋግሞ ሲደውል ነበር። አላነሳሁለትም። ይሄ አሳማ! ጨምሩ ሊላለን ነው መሰለኝ። ?"ሲልሽ ወደ ፈዛዛው ፣ ደብዛዛው፣ ለዛዛው መደበኛ ትዳርሽ ተስፈንጥረሽ ትመለሻለሽ።
ሁለት)
ካልተጣላችሁ ትፋታላችሁ!
ይሄን ስልሽ ደግሞ ዘወትር በነገር ተቋሰሉ፣ ነጋ ጠባ ጠበኛ ሁኑ እያልኩሽ አይደለም፡፡ ግን የሚዋደድ ባልና ሚስት አልፎ አልፎ ካልተጋጨ፣ ቀን እየዘለለ ካልተደባበረ፣ ተደባብሮ ካልታረቀ፣ ታርቆ እንደገና ካልተደባበረ….ነገር አለ!
ተጣላችሁ ማለት ትፋታላችሁ ማለት አይደለም፡፡
ይልቁንም ነገርን እያድበሰበሱ በሆድ ይፍጀውና በችዬው ልኑር በከመሩት ቁጥር ክብደቱ ከመጠን ያልፍና ወገብም ቅስምን ሰብሮ ባልጠበቁት ሰአት ትዳሩን ይበትነዋል፡፡
እንደ ተቀበረ ቦንብ የት ጋር ነበር ሳይባል ፈንድቶ ሁለታችሁንም ይበታትናችኋል፡፡
ስለዚህ መሰረታዊ ባልሆነ ነገር ጊዜያዊ ጠብ ብትጣሉ አትሸበሪ፡፡
ይልቅ ካልተጣላችሁ..ለመጣላት እንኳን ግድ ካልሰጣችሁ … ያኔ….እሱን ፍሪ!
ሶስት)
ባልሽን ሳታቋርጪ ስትነተርኪው ምንም ካልመለሰልሽ የምትይውን ማዳመጥ ካቆመ ቆይቷል።
አለ አይደል….አንቺ ሳይከፍል ስለረሳው የልጆች የትምህርት ቤት ክፍያ ስትለፈልፊ እሱ አርሴናል እኔ ሳልሞት ዋንጫ ይበላ ይሆን ብሎ እያሰበ፣ አውራ ዶሮ ግን ከረቫት ቢያደርግ ምን ትመስል ይሆን በሚል የቂል ሃሳብ ራሱን እያዝናና ነው።
ይሄ ደግሞ ክፋት አይደለም፡፡ ወንድነት ነው፡፡ አንቺ ፊትሽ እንዳይጨማደድ ሞይስቸራይዘር እንደምትለቀለቂው እሱም ይሄን ሲያደርግ ራሱን እየጠበቀ ነው- በወንድኛ!
፪) ባልሽ ምን አንጀትሽን ቢበጥሰው….(እመኚኝ ደህና የሚባለው ባል እንኳን ደጋግሞ ይበጥሰዋል) አፀፋውን ልመልስ ብለሽ ካንቋሸሽው፣ በሰው መሃል ካዋረድሽና ካሳንሽው፣ ወይ ደግሞ ሲደክም በማበርታት ፈንታ ልግመኛ ካልሽው፣ ሲከፋው እንደማፅናናት ሆድ ብሶት ሳለ ማጭድ ካቀበልሽው፣ ሲጎድልበት ከተሳለቅሽበት፣ ሲወድቅ ከረገጥሽው፣ ለሸረኛና አሽሟጣጭ ሰው አሳልፈሽ ከሰጠሽው፣
እንደው ባጠቃላይ ባሌ ነው ብለሽ የመረጥሽውን ሰው እንደልቤ አልሆነልኝም ብለሽ የወንድነት ክብሩን ከነካሽው፣ የአባወራ ማእረጉን ግፍፍ አድርገሽ ካኮሰስሽው
እቱ ገላ! ሁሉ ነገር ማክተሙ ነው።
በቃ ምን ልበልሽ?
ባልሽን እንዲህ ያለ ነገር (በተለይ ደጋግመሽ ) ከሰራሽው
የጎጆሽን ስርና መሰረት ነቀነቅሽው።
አራት)
ባልሽ ( ልክሽ ባይሆንም፣ አንቺ ለራስሽ የማትመርጪው ነገር ቢሆንም፣ ባትወጂውም) አስቦ ስጦታ ቢጤ ሲያመጣልሽ፣ ያላሰብሽውን ሸክም ሲያቀልልሽ አቅፎ በማመስገን ፋንታ ቆሌውን ከገፈፍሽው ….ቢፋቅ ቢፋቅ የማይደበዝዝ ደማቅ ስህተት ሰራሽ።
አለ አይደል…
ስጦታውን እያየሽ…
ሲያስጠላ!
ምን ሆነህ ነው ይሄን የገዛኸው?
ርካሽ ነው አይደል?
አንድ ነገር ሲፈጽምልሽ ፣
ድሮስ ማን ሊሰራልህ ነበር?
ምናምን እያልሽ ቅስሙን አትስበሪው፡፡
ለምን አትይም?
ወንድ ልጅ ከውጪ ሲታይ የአዞ ቆዳ ይኑረው እንጂ ውስጡ እምቡጥ ነው፡፡
ጥሩ የሰራ ሲመስለው፤ ከምንም በላይ ጎሽ መባልን፣ በሚስቱ መመስገንን፣ ከባለቤቱ አበጀህ የኔ አንበሳን የሚሉ ቃላትን ይናፍቃል።
ይሄንን በፌኒዝምኛ ስታወራርጅው ባይጥምሽም ዋጭው።
ስለዚህ የባልሽን ስጦታና ድርጊት እንዳልወደድሽው ወይ እና እንዳልተስማማሽ መንገር ቢኖርብሽ እንኳን የተሻለ ጊዜና ሁኔታ ምረጪ።
እንዴት ልበልሽ…በክፉ ቃላት ሰብረሽው ትዳርሽን ከማመስ ይልቅ ያምራል ብሎ የገዛልሽን የስልሳ ዓመት ባልቴት የሚያስመስልሽን ዥንጉርጉሩን ገርዳሜ ቀሚስ ለአንዲት ቀን ለብሰሽ ከአይኑ ብትሰውሪውና ቆይተሽ በመላ…እኔ የምወደው ቀሚስ እኮ እንዲህ ያለ ነው ብትይው አይሻልም?
ከፋሽ እንዴ?
አይክፋሽ።
እመኚኝ ይህንን ሁሉ ቀድመሽ በማወቅሽ በኃላ ከሚመጣ የከፋ የልብ ስብራት ትድኛለሽ።
ልደምድምልሽ።
ምን መሰለሽ?
ትዳር እንከን አልባ ሰውን ፍልጎ በማግባት የሚቆም ለደስታና ለጨዋታ ብቻ የተሰራ ተቋም አይደለም።
እንዳይጎረና የሚማሰል ወጥ፣ እንዳይደርቅ የሚኮተኮት የአትክልት ስፍራ፣ እንዳይታመም የሚከተብ ሕይወት ያለው ነገር ነው፡፡
ቅዳሜ ቀትር ላይ፡፡
ባለትዳሮች ቤት፡፡
እሷ- ዛሬ ቅዳሜ ነው፡፡ በዚያ ላይ ውጪ ከበላን ስንት ጊዚያችን! እስቲ ምሳ ጋበዘኝ?
እሱ- ደስ ይለኛል፡፡ የት ልውሰድሽ?
እሷ- እ…ታቦር ጋር ሸክላ ጥብስ ብንበላስ?
እሱ- አሪፍ! በይ ቶሎ ልበሺና እንሂዳ..አርፍደን ደህና ስጋ እንዳናጣ፡፡
እሷ- እሺ…ማሬ…ከምሳ በኋላ ሌላ ቦታ ሄደን አሪፍ ቡና ትጋብዘኛለህ፡፡
እሱ- ታቦር ጋር ምን የመሰለ ቡና አለልሽ አይደል…? ሁሌ የምታደንቂው ቡና ከነጭሱ፡፡ በልተን ስንጨርስ እዛው ብትጠጪስ?
እሷ- እሱማ አሪፍ ቡና አላቸው ግን ያው ከወጣን ላይቀር ቤት ቀይረን ትንሽ እንድንዝናና..ፈታ እንድንል ብዬ ነው…
እሱ- አሪፍ ቡና ከፈለግሽ የምታውቂው ቦታ እያለ…ለዚያውም እዛ ምሳ እየበላን ለምን ሌላ ቦታ እንንከራተታን ብዬ እኮ ነው፡፡
እሷ- አንተ ደግሞ… አዲሳባ የጀበና ቡና እዚያ ብቻ ነው እንዴ ያለው..? ምን ችግር አለው ዞር ዞር ብንል…ትንሽ ንፋስ ቢመታን?
እሱ- በዚህ ፀሃይ ንፋስ ነው ጸሃይ የሚመታን…?እንግልቱ አይበልጥም?
እሷ-እኔ እኮ የሚገርመኝ… ለምንድነው ቀላሉን ነገር የምታወሳስበው…? እዚያ ምሳ በልተን ምናለ ሌላ ቦታ ሄደን ቡና ብንጠጣ…? ተሸከመኝ አላልኩህ…በራሴ እግር ነው የምሄደው…፡፡
እሱ- ሆይ ሆይ….እኔ አሁን እንደዚያ ወጣኝ..? በይ እሺ ቶሎ ልበሺና እንሂድ…ደስ እንዳለሽ እናደርጋለን፡፡
እሷ- ኤጭ! ተወው እንደውም
እሱ- እንዴ…ምኑን የምተወው…?
እሷ- ምሳውን…መውጣቱን…
እሱ- እንዴ ለምን…?
እሷ- ደግሞ ለምን ትለኛለህ…እየተነጫነጭክ ይዘኸኝ ከምትወጣ ቢቀርብኝ አይሻልም…? ይሻልሃል፡፡
እሱ- ኦኬ! ደስ እንዳለሽ….
እሷ- አየህ…ትንሽ እንኳን ልታባብለኝ ልታግደረድረኝ አልሞከርክም…
እሱ- እንዴ!
እሷ- አስሬ እንዴ እንዴ አትበልብኝ…መውጣት ካልፈለግህ መጀመሪያውኑ እምቢ…አልፈልግም አትልም…
እሱ - --------
እሷ- በል ተወው…የትላንቱን ሹሮ አሙቄ እበላለሁ…ሰው ሲሸልስ ሄዶ ቢች ዳር ይጋበዛል ለእኔ የሰፈር ጥብስ አረረብኝ…. እርግማን አለብኝ መቼስ…አትዝናኚ…አትደሰቺ ..እርር እንዳልሽ ሙቺ የሚል…
እሱ- -------
By Hiwot Emishaw
@wegoch
@wegoch
@paappii
አንድ አስናቀች
(ገብርኤላ ይመር)
እንደ ኑሮአችን እነርሱም ተደጋግፈው ከተሰሩት ከምኖርባት መንደራችን በአዲስ ዓመት ጠዋት ላይ አበባይሆሽ የሚጨፍሩ ልጆች ድምጽ ከተንጋለልኩበት ፍራሼ ላይ ሆኜ በስሱ የከፈትኳትን ሙዚቃ ሰብሮ ገርብብ ያለ በሬን አልፎ በጆሮዬ ዘለቀ
"የመስቀል ለታ
የደመራው
ንፍሮ ቀቅዬ ብላ ብለው ጉልቻ አንስቶ ጎኔን አለው ከጎኔም ጎኔ ኩላሊቴን እናቴን ጥሯት መድሓኒቴን እሷን ካጣችሁ መቀነቷን አሸተዋለሁ እሷን እሷን..." ይላሉ።
ኩላሊቴን ሳይሆን ልቤን ካለው ነገር እንደ ወጌሻ የእናት ፍቅሯ አሽቶ እንዳይጠገኝ እናትዬ ካረፈች ልክ 3 ዓመቷ ነው። እርሷን እርሷን የማሸተው መቀነት ባትተውልኝ ዘመኗን አብሪያት ስኖር የምትከፍታት አስናቀች ወርቁ ስቀመጥ፣ ስነሳ፣ስተኛ ስጓዝ እሰማታለሁ፣ በትዝታ ክራሯ አንጀቴን እየከረከረች፣ ከምናፍቃት እናቴ እቅፍ ትጥለኛለች።
ከአመሻሽ ገበያተኛ መኖሪያችንን ልትቃርም ወደ ጉሊቷ ልትመለስ ስትል "እንቅልፍ ጥሎሽ ማደሪያ እንዳታሳጪኝ ሳትሸነቁሪ ገርበብ አርገሽ በሩን ተይው እሺ " ትለኝና ፣ መለስ ብላ ደግሞ "እንዳይደብርሽ ቴፑን ክፈቺ" ብላኝ እስክትመጣ የተገረበበ በሬ ላይ ዓይኔን ጥዬ ከአስናቀች ወርቁ ጋር የምጠብቃት፣ ተመልሳ ለራታችንን የሚሆን ስታዘገጃጅ ከጎኗ ተቀምጬ የእርሷን ወግና አስናቀችን እኩል እየቀዳሁ ዝም ብዬ የማያት፣ ስነሳ እንደ ጠዋት ዜና ከቁርሳችን እኩል ት/ቤት እስክሄድ የምሰማት፣ እናቴ ስትደሰት፣ ስታዝን፣ ስትሰራ፣ ስትቆዝም ሁሉ ከዚህች ሴት ወዲያ የማታውቅ የምትመስለኝ እንደውም ዘመድ ረግጦት የማያውቅ ቤታችን ውስጥ አስናቀችና ክራሯ የልብ ዘመዶቻችን ነበሩ።
አሁንም በትመጣ እንደው ገርበብ ያረኩት በሬ ኩላሊቴን ሳይሆን፣ ልቤን ወዳለው ሰው በረርኩ።
ሳገኘው ሁለተኛ ዓመት የግቢ ተማሪ ነበርኩ።
እንደለመድኩት ኤርፎኔን በጆሮዎቼ ከትቼ አስናቀችን እየሰማሁ፣ ቦርሳዬን ይዤ ልወጣ ስል በአንዱ አልጋ ከላይ ጸጉሯን እየሰራች ያነበረችው ማሂ " እንደለመድሽው ገርብብ አድርገሽ ሄደሽ ከዚህ እንዳታስወርጂኝ ፣ በሩን ገጥመሽ ዝጊው አለችኝ ፈገግ ብላ በፍጹም ሰው ካላስታወሰኝ በቀር በር እስከመጨረሻው ዘግቼ አልወጣም፣ እንደ እናትዬ ገርበብ እንዳለ ነው የምተወው እንደኔ በተስፋ የሚጠብቀኝ ካለ ብዬ ይሆናል።
በሩን እንዳለቺኝ ገጥሜ ከላየረብሪው ስደርስ ከውስጥ በፍጥነት እየተመናቀረ የሚወጣ ልጅ ገፈታትሮኝ በእጄ ያለውን ስልክ አስጣለኝ
"ቀስ አትልም? ያምሀል" ልለው ስዞር ቀድሞኝ "ያምሻል" ብሎ እየጠራ ያለው ስልኩን አንስቶ ወደ ላይ ሄደ
በሆዴ "ሆ ያምሻል? " አልኩና የወደቀ ስልኬ ደህና መሆኑን አገላብጬ አይቼ ወደ ለመድኩት ቦታዬ ስሄድ ተይዞ ተበቀኝና ከአጠገቡ ካለው 4 ሰው የሚያስቀምጥ ወንበር ሄጄ ከፊትለፊቴ የተከፈተ ላፕቶፕ ቦርሳውን ዞር አድርጌ ተቀመጥኩ። ትንሽ ቆይቶ ወዳለሁበት ወንበር በፍጥነት እርምጃ የደረሰ፣ የሚያለከልክ ልጅ ተቀመጠ። ያ የገፈተረኝ። ራሱ ገፍትሮ ደርሶ ያምሻል ማለቱ አናዶኝ ነበርና ፊቴን አጠቆርኩ እርሱ ግን ሀሳቡ ሁሉ በስልኩ ላይ ነበርና የሆነ ነገር ሊሰማ ወደ ጆሮው ሲያስጠጋ አልሰማ ስላለው ያጠቆርኩበት ፊቴን ሳያይ ላፕቶፑ ላይ የተሰካውን ኤርፎን ሲነቅለው ሲሰማ የነበረው ሙዚቃ ላይብሪውን አመሰው።
በራኬብ ቤት እንደተንጠለጠለ ቀይ ግምጃ የጠላው ውቃቢዬን አባሮ መውደድ ሰፈረበት፣ "ያመሃል እንዴ" ብላ በጩኸት እንደ ኢያሪኮ ልታፈርሰው የነበረች ምላሴን መሰብሰቤ በጀኝ። እንደ ራኬብ ከመፍረስ የሚታደገው ቀይ ግምጃ ከላፕቶፑ ወጣች ።አስናቀች ወርቁ
ፈገግ አልኩ
ሰው ሁሉ ወደርሱ በማየቱ አይኖቹን የሚያሸሽበት ነገር ሲፈልግ ፈገግ ብለው የሚያዩት ዓይኖቼ ላይ አረፈ።
ግራ በተጋባ ፊቱ ገረመመኝና፣ የተከፈተውን ለመዝጋት አቀረቀረ።
"ደህና ነህ "አልኩት ቀስ ብዬ
ከሰው ጋር ገጥሞ አለማውራቴ ጉድ ባስባለበት ግቢ የማላውቀውን ልጅ ደርሼ ደህና ነህ ማለቴ ጉድ ነበረ።
ከዚያ ቀን በኋላ ከዚያች ወንበር ከፊትለፊቱ መቀመጥ ልማዴ ሆነ። በመተያየት፣ ሰላምታ፣ ከሰላምታ ወደ መጠያየቅ ወደ መተዋወቅ ተሻገርን። በላይብሪ የታጠረ ድንበራችንን ሰብረን የቀንተቀን ጓደኛ ሆንን
"የት ነሽ?" ለሚለው ጥያቄ
"ሱራፌል ጋር "የሁልጊዜ መልሴም ሆነ።
ብዙውን ጊዜ የዛ ቀን እርሱንም ልቡንም ስላመናቀረችው ቤዛ የምትባል ሴት ይነግረኛል፣ ልክ የእናትዬን ወግና አስናቀችን ዝም ብዬ እንደምሰማ ሁሉ እንዴት፣ ወዴት፣ መቼና ምን ሳልል ዝም ብዬ እሰማዋለሁ። አውርቶኝ፣ አውርቶኝ ሲበቃው "አውርተሽኝ አታውቂም አውሪኝ እንጂ" ይለኛል። ዝም እለዋለሁ። እጆቼን ይይዝና "ነገ ስንገናኝ አንቺ ነሽ የምታወሪው" ይለኝና የያዛቸው እጆቼን ከዛ ግንባሬን ይስመኛል ። ዝም ብዬ አየዋለሁ። "ከመሄዳችን በፊት ግን አንድ አስናቀችን" ብሎ አንዱን የኤርፎን ጆሮ ይሰጠኛል። ትከሻው ላይ ራሴን ጥዬ፣እርሱ በጸጉሮቼ እየተጫወተና ለምን ለእርሱ የምትዘፍን እንደሚመስለው እየነገረኝ ዳግም እንደ እናትዬ የእርሱን ወግ ከአስናቀች ጋር አደምጣለሁ።
እኔ ዝም ብሎ በማዳመጥ ብኖርም ግን ህይወት ዝም አትልምና የት፣ ምን፣ እንዴት ያላልኳት ቤዛ ዳግም ተመለሰች። እንዲሁ አንድ ቀን ከመሄዳችን በፊት አስናቀችን እየሰማን ስልኩ ጠራ አየሁት "ቤዝዬዬዬዬዬ" ይላል ብዙ ዬ ነበረው። ከስልኩ የነበረቀውን ኤርፎን ነቅሎ ሊያወራት ከኔ ራቅ አለ። ከዚያች ቀን በኋላም ከእኔ ራቅ ራቅ እያለ ሄደ ። እኔም በኋላ ማናት ብዬ መልኳን እንኳን ለማየት ያልጠየኳት ቤዛን አወኳት፣ አብረው። ወትሮ ነገርን መዝጋት የማያውቀው ጎኔ ባስለመደኝ ሰዓት እስኪደውል እጠብቃለሁ፣ በየሄድንባቸው ቦታዎች ልክ እንደናትዬ እስኪመጣ አያለሁ ግን አልነበረም። እርሱ ገርበብ አድርጎ የጠበቃት ፍቅሩ ስትመለስ፣ የኔን በር ገርበብ አድርጎት ሄደ።
ሶስተኛ ዓመት ከዛም ወደ መመረቂያ ዓመቴ ስገባ ገርበብ ያረኩትን ልቤን ለራሴ ስል ዘጋሁት። ግን እሰማለሁ "ቤዛ እኮ ጥላው ሄደች በናትሽ የታባቱ" የዶርሜ ልጆች እኔን ሊያስደስቱ እየተሳሳቁ ያወጉኛል። ዝም።" ደግሞ ሌላ ሴት ይዟል ማን ነው ስሟ" ይጠያየቃሉ። ዝም።
የቤዛን እጆቿን አይዛትም ነበር ፣ በጸጉሮቿ አይጫወትም፣ በመሀላቸው ገርበብ ያለ ክፍተት አለ፣ ሌላም ካሏት፣ ከሌላዋም፣ ከቀጣየም አብሯቸው ሆኖ አየዋለሁ ፣ በሴቶቹና እሱ መሀል እንደ በሬ የተገረበበ ክፍተት አለ። ዝም። ባለበት ቦታ ካለሁ ዓይኖቹ ግን የሆነ ነገር ሊሉኝ በመፈለግ እኔ ላይ ናቸው።
የመመረቂያ ቀናችን ደርሶ፣ ተመርቀን እንደ ነገ ልንሄድ እንደ ዛሬ ከግቢው ቡና ቤት ተሰይመናል። በአንድ ጓደኛችን ስልክ እዛው ካለው ሞንታርቦ ስልኩን አገናኝተን ሙዚቃ እየከፈትን የስንብት እንጨዋወታለን። የነርሱ ዲፓርትመንት ለመመረቅ ሁለት ዓመት ቢቀረውም እግር ጥሎት ከጓደኞቹ ጋር እኛ ከተቀጥንበት ፊትለፊት መጥቶ ተቀመጠ። ዓይኖቹ ሰውነቴ ላይ እንደሆኑ አውቄዋለሁ ግን ወደ ማብቃቱ አካባቢ ከመሄዳችን በፊት" አንቺ የምትፈልጊው ሙዚቃ የለም?" አለኝ ስልኩን ከሞንታርቦ ጋር ያገናኘው ጓደኛችን። ያለችኝን አንድ አስናቀችን ላኩለትና ከፈታት። ቀና ብዬ ፊትለፊት አየሁ፣ አየኝ እስከ መጨረሻው ከመሄዴ በፊት አንድ አስናቀች። በዝምታ
By Gabriela
@wegoch
@wegoch
@paappii
ይህም ባህሌ ነው
ከሃያ ስድስት አመት በፊት፣ ገና ወደ ሆላንድ እንደመጣሁ ጓደኞቼ 'አምስተርዳም ውስጥ የምናሳይሽ ድንቅ ነገር አለ' ብለው ይዘውኝ ሄዱ። ከሮተርዳም በባቡር የ45 ደቂቃ መንገድ ተጉዘን እስክንደርስ ድረስ እነዚህ በሰው በሰው ያወቅኳቸው ሃበሻ ጓደኞቼ “የነጮቹን ጉድ ታያለሽ---” እያሉ እስክንደርስ ድረስ ልቤን በጉጉት ሰቀሉት። አይደረስ አይቀር Red light destrict የሚባል ቦታ ደረስን። ሴተኛ አዳሪዎች በተገለጠ መስታዎት ውስጥ ጡት ማስያዢያ እና የውስጥ ሱሪ ብቻ ለብሰው ሰው በሚያማልል አኳኋን ተቀምጠው ሚውዝየም እንደሚታይ እንሰሳ ወይም ዕቃ በጎብኚዎች ይታያሉ። አየሁ፣ ዞር ዞር ብዬ የሚያይዋቸውንም ቃኘሁ፣ የነጭ ገላ እንዲህ ተገላልጦ ሳይ የመጀመሪያዬ በመሆኑ በመጠኑ ተገረምኩ። ነገር ግን ጓደኞቼ እንደጠበቁት በጣም አልተደመምኩም። አለመደንገጤ ወይም በስመአብ ብዬ አማትቤ አገሬ መልሱኝ አለማለቴ አወዛገባቸው። ከጎኔ እየተራመደች ስትመራኝ የነበረችው ጠይሟ ፍንጭት ልጅ “ከባህላችን ጋር ስለማይሄድ ብዙ ሃበሾች ይደነግጣሉ” አለችና መልስ ፍለጋ ትቃኝኝ ጀመር። ነገሩን አይቼ አለማጋነኔ ያበሳጫት ትመስል ነበር። አልፈረድኩባትም። ግን ምን ልበላት?
አኔ፣ ትግስት፣ የቤት ስሜ ሚሚ፣ የአቶ ሳሙኤል ማቴዎስ በቀለ ልጅ፣ መርካቶ ከፍተኛ 5 ቀበሌ 17 የቤት ቁጥር 475 ነበር መኖሪያዬ ልበላት? ከሰፈሬ አንድ አስፋልት ከፍ ብሎ የነበረው የሴተኛ አዳሪዎች ሰፈር ቀበሌ 12 ይባል ነበር ልበላት? ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ያጠናቀቅኩት አዲስ ከተማ ትምህርት ቤት ነው ልበላት? ከቤቴ ወደ ትምህርት ቤቴ ለመድረስ በ12 ቀበሌ ሰፈር ውስጥ ውስጡን ስጓዝ ያልተሳለምኩት ሴተኛ አዳሪ አልነበረም ልበላት? አንዷ በጉርድ ቀሚስ፣ አንዷ በቀይ ጫማ፣ አንዷ በውሰጥ ልብስ፣ አንዷ ስትታጠብ፣ አንዷ ስትቀባ፣ አንዷ ስታማልል ጠባብ ሱሪ አጥልቃ፣ አንዷ በጠዋቱ፣ አንዷ በከሰአት፣ አንዷ አመሻሽ ላይ፣ በነጻነት ቆመው ሁሉን አይቻለሁ ልበላት? የትዬ እንትና ባል፣ ያ ጠጅ አዘውታሪው፣ 3 ቀን ሙሉ ተፈልጎ ጠፋ። ሚስቲቱ ሰክሮ ቦይ ውስጥ ወድቆ ሞቷል ብላ ተንሰቅስቃ አለቀሰች። የሰፈሩ ሰው ተገልብጦ ወጥቶ ባልየው ሲፈለግ፣ የ12 ቀበሌዋ ሴተኛ አዳሪ ስላጽ “አኔ ጋር ነው ግን አልከፈለኝም” ብላ ያሳበቀች ዕለት፣ ሰውዬው ተጎትቶ ከቤቷ ሲወጣ፣ እኔም እዛ ነበርኩ ልበላት?
አባቴ የአትዮጵያ አየር መንገድ ይሰራ ስለነበር የተለያዩ አገሮች ለስራ ሲጓዝ የሚሸጡ አልባሳትና ጫማዎች ያመጣ ነበር። አንድ ጊዜ ከታይላንድ ሲመለስ ብዙ የሚሸጡ ቦርሳዎች አምጥቶ ለእናቴ እና ለእህቶቹ ሸጠው አንዲያተርፉ አከፋፈላቸው። በጣም የምወዳት አክስቴ አራት ቦርሳ አስይዛኝ ወደ ሴተኛ አዳሪዎቹ ሰፈር ላከችኝ። ትጠብቅሻለች የተባልኩት ስሟን በቅጡ የማላስታውሰው ቀይ ዳማዋ ሴተኛ አዳሪ ቤት ስደርስ ከደንበኛዋ ጋር ነበረች። በጣም ያረጀ፣ አውራ ጣቱ ጫፍ ተበላልቶ የተቀደደ፣ ቡናማ የወንድ ቆዳ ጫማ አልጋው ስር ይታያል። ከንፈሩ ሳይሳም ከሚያድር ቢታረዝ የሚመርጥ ሰውዬ አልጋዋ ላይ እደነበረ ከጫማው ገምቼ ነበር። በመጋረጃ ከተከለለው አልጋዋ ተስፈንጥራ ወጥታ ይዤ የነበረውን አራቱንም ቦርሳዎች አንድ በአንድ ቃኝቻቸው። ከመጋረጃው ጀርባ ሰውዬው በስሱ ያስላል። የቱን እንደምትመርጥ ዓይንአዋጅ ሆነባት መሰለኝ በርጩማ ላይ አስቀምጣኝ ትንሽ እንድጠብቃት አዝዛኝ ወደ ደንበኛዋ ተመለሰች።
ታዲያ የአምስተርዳም አስጎብኚዬን ምን ልበላት? እኔ ትግስት፣ የአቶ ሳሙኤል ማቴዎስ በቀለ ልጅ፣ አንዲት የቀይ ዳማ ሴተኛ አዳሪ በመጋረጃ ተከልላ ከደንበኛዋ ጋር አንሶላ ስትጋፈፍ አኔም እዛው ክፍል ነበርሁ ልበላት? አራት ከታይላንድ የመጡ ቦርሳዎች አቅፌ፣ እሱ ዚፑን ሲከፍት፣ የአልጋ ላይ ግብግብ፣ አሷ ስታቃስት፣ እሱ ሲያለከልክ፣ እንዳልተቃኝ ማሲንቆ የሽቦ አልጋዋ ሲያለቅስ ሰምቻለሁ ልበላት? በኋላም ሰውዬው ከመጋረጃ ጀርባ ሲለባብስ፣ ከፍሎ ሲወጣ ትዝ የሚለኝ ጀርባው ነበር። ደርዙ የተተረተረ ሱሪው .... ልበላት? አጠገቤ መጥታ እንደገና ቦርሳ ስትመርጥ፣ የሩካቤ ምርቃናዋ ሳይበርድ፣ ላብ ያዘፈቀውን ሰውነቷን አይቻለሁ ልበላት? ይህም ባህሌ ነው ልበላት?
By ትግስት ሳሙኤል
@wegoch
@wegoch
@paappii
ከአዲስ አበባ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ የሚመበር የኢትዮጵያ አየር መንገድ ላይ ከባለቤቴ ጋር የተመደበልልን ቦታ ቀደም ብለን ይዘናል፡፡
ግዙፉ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለቀጣይ አሰራ ሁለት ሰዓታት ለሚያደርገው ጉዞ ዝግጅቱን አጧጡፎታል፡፡
እኔና ባለቤቴ መቀመጫችንን የሚጋራውን ሶስተኛውን ሰው ስንጠብቅ አንዲት በአምሳዎቹ መጨረሻ ላይ የሚገኙ ሰው ከተፍ አሉ፡፡ በእጃቸው ከዘራ በሌላኛው እጃቸው የሚጎተት ሻንጣ ይዘዋል፡፡
ሻንጣቸውን ከላይ የሚገኘው ማስቀመጫ ላይ እንዳኖርላቸው ለጠየቁኝ እርዳታ ፈጠን ብዬ ተቀብዬ ሰቀልኩኝ፡፡
ምስጋናዬን ተቀብዬ ከመቀመጤ መዳረሻችን ስንደርስ ካወረድክላቸው በኃላ ላግዞት፣ ልግፍ አንዳትል አለች፡፡
ደግሞ ምን ችግር አለው፡፡ የሀገሬ ሰው ባግዝ፡፡ አንድ ሁለት ተባባልን፡፡
ቀጥላ ይህንን የአንዲት ተሳፋሪ ታሪክ አጫወተችኝ፡፡
አንድ መዳረሻውን ዱባይ ያደረገ አውሮፕላን ውስጥ ከእኔ ቀጥሎ አንዲት ተለቅ ያለች ሴት ትመጠጣና የያዘቸውን የእጅ ቦርሳ ከላይ ባለው የእቃ ማስቀመጫ ላይ እንዳኖርላት ትጠይቀኛለች፡፡ ነገር ግን ከእኔ ትይዩ ተቀምጦ የነበረው ሰው ቀልጠፍ ብሎ ተቀብሎ የተጠየኩትን ድጋፍ አደረገ፡፡
ሴትዩዋ ከጎኔ መቀመጫዋን ካመቻቸችና መታጠቂያ ቀበቶዋን ካሰረች በኃላ አክብሮት የተሞላ ወሬ ጀመረችኝ፡፡ በረራችን አንደተጀመረ ብዙም ሳንጓዝ ሆዷን ቁርጠት እንዳጣደፋት ነገረችኝ፡፡ የበረራ አስተናጋጅ ጠርቼ አባካችሁን እርዷት አልኩኝ፡፡ እነሱም መጥተው ድጋፍ አደረጉ፡፡ ከዚያች ቅፅበት ጀምሮ ሴትዩዋ ልጄ እያለች እኔን መጥራት ጀመረች፡፡ ያው ላደረጉት ነገር ይሆናል ብዬ ተቀበልኩ፡፡ ሁሉም ሰው አብረን እንደሆንን ማሰብ ጀመረ፡፡
ልክ ዱባይ ስንደርስ መጀመሪያ ሻንጣውን በማስቀመጥ የረዳት ሰው ሻንጣውን ካወረደላት በኃላ ወደእኔ ጠጋ ብሎ በፍጥነት ከሴትዮዋ እንድርቅና ለበረራ አስተናጋጆቹ አብረን እንዳልሆንን እንዳሳውቃቸው ነገረኝ፡፡
ማስጠንቀቂያው ዋጋ አልነበረውም፡፡
የበረራ አስተናጋጆቹ ከሴትዮዋ ጋር ያለንን ግንኙነት ጠየቁኝ፡፡ እዚሁ አውሮፕላን ላይ መገናኘታችንን ተናገርኩ፡፡ ሴትዮዋ የእጅ ቦርሳዋን እንዳግዛት ለመነችኝ፡፡ ትንሽ ተወዛገብኩ፡፡ ያ ሰው በምልክት እንዳላግዛት አልፎም የበረራ አስተናጋጆቹ አገዛ መጠየቅ እንደሚቻል በቃል ተናገረኝ፡፡
ስሜቱ ቀላል አልነበረም ድንገት የታመመ ሰው አግዙኝ ሲል ጥሎ መሄድ ግን የሰውየውን ምክር ተቀብዬ ዊልቼር እንድትጠብቅ አድርጌ ትቻት መራመዴን ቀጠልኩ፡፡ በደቂቃዎች ውስጥ ከባድ ረብሻ ተፈጠረ፡፡ ከመጣላት ዊልቸሩ ላይ ቦርሳዋን ይዛ ለመራመድ ስትሞክር የኤርፖርት ፖሊስ በቁጥጥር ስር አዋላት፡፡
ከመቅፅበት ልጄ ልጄ እያለች ወደእኔ መጣራት ጀመረች፡፡ ጥያት እየሄድኩ እንደሆነ ወነጀለችኝ፡፡
ለካንስ ሴትዮዋ ከህገወጥ አደንዛዥ እፅ ዝውውር በተያያዘ ተይዛ ነው፡፡
እኔም ተያዝኩ፡፡ የሆነውን አስረዳው፡፡ ፖሊስ ሙሉ ስሜን እንድትናገር ጠየቃት፡፡ መጥራት አልቻለችም፡፡ ቦርሳዬ ተበረበረ፡፡ አሻራዬ ተመሳከረ፡፡ ምንም አይነት ትስስሮች ማግኘት ስላልተቻለ በመጨረሻ ነፃ ወጣው፡፡
ይህ ገጠመኝ በህይወቴ ትልቁን ትምህርት አስተማረኝ፡፡ በጉዞ ላይ ምንም አንኳ ሰውን መርዳት ጥሩ ቢሆንም ቅሉ የራስ ሻንጣ የራስ ነው፡፡ የሰው ሻንጣ ደግሞ የሰው፡፡
ታሪኩን ሰምቼ ስጨርስ ከጎኔ የተቀመጡትን ሴትዬዋን ተመለከትኩ፡፡
ከአስራ ሁለት ሰዓት በረራ በኃላ ስንደርስ አንደመጀመሪያው ሳይሆን በግማሽ ልቤ የሰቀልኩትን ቦርሳ አውርጄ ሰጠውኝ፡፡
አመሰገኑኝ፡፡
የገረመኝ መዳረሻችን የሆነው Washington Dulles International Airport የተቀበለን ባለማቋረጥ የሚነገረው የሰው ሻንጣ እንዳትይዙ፣ እንዳትረዱ . . . የሚለው ማስጠንቀቂያ ነበር፡፡
መልካም ሁኑ ግን ህይወታችሁ መልካምነታችሁን ብቻ ዋጋ ሊያስከፍለው ይችላልና መጠንቀቁ አይከፋም፡፡
ደግ አይለፍችሁ❤️
@wegoch
@wegoch
@paappii
By Tesfaye Haile
መተውን የመሰለ ነገር የለም!
(አሌክስ አብርሃም)
ይታያችሁ ሴቶች በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በቀን ብዙ ጊዜ የሚነካኩት የሰውነታቸው ክፍል ምናቸውን ይመስላችኋል? (ወንዶች አትባልጉ በቃ ከሱ ሌላ ሀሳብ የላችሁም?) ፀጉራቸው ነው። በትንሹ በቀን ከ96- 140 ጊዜ ይነካኩታል ይላል አንድ ጥናት። ምን ይሄ ብቻ አንዲት መደበኛ ሴት ፀጉሯን እንደነገሩ ለመንከባከብ (መታጠብ ፣ ማድረቅ መፈሸን ወዘተ) በሳምንት በትንሹ 9 ሰዓታትን ስትወስድ ለውበት ከፍ ያለ ቦታ የምትሰጥ ሴት ደግሞ እስከ 16 ሰዓት ታጠፋለች። በወር ካሰላነው 64 ሰዓት በዓመት 768 ሰዓት ማለት ነው። እንደኛ ባለው አገር የፀጉር ቤት ወረፋ ሲደመርበት የትየለሌ ነው። ይሄ የጊዜ ጉዳይ ነው ወደገንዘብ ከመጣን ለሻምፖ ኮንዲሽነር፣ የተለያየ ትሪትመንት፣ ለቀለም፣ ለቅባት፣ ለፍሸና አንዲት ሴት የምታወጣው ወጭ ጆሮ ጭው ያደርጋል። ይሄ ሁሉ ሆኖ አሳዛኙ ነገር የሴቶች ፀጉር ካለፉት አምስት አስርተ ዓመታት ጋር ሲነፃፀር ጥንካሬው ብዛቱ እና ርዝመቱ በግማሽ ቀንሷል። ይህም ከመዋቢያ ኬሚካሎች፣ ከአየር ፀባይ ፣ ከአመጋገብ፣ ከውሃ ከአኗኗር ስታይልና እና ረፍት ከማጣት ጋር ይያያዛል። እና ምን ተሻለ ....ተማር ያለው ከዙሪያው ይማራል፤ የአውሮፓን ዴርማቶሎጅስቶች ዝብዘባ ተውትና ወዲህ ተመልከቱ!
ሰሞኑን "የኦነግ ሸኔ አባላት የነበሩ እጅ ሰጥተው ወደሰላም ተመለሱ" የተባሉ ሰወችን አይተናል፣ እነዚህ ሰወች በዱር በገደል ከረሙ የተባሉ ፣በጦርነት ያለፉ ወዘተ ናቸው እንደተነገረን። በሚገርም ሁኔታ ግን ከተማ ሴቶቻችን በፆም በፆሎት፣ በዘመነ ትሪትመንት ኢንች ማስረዘም የተሳናቸው ፀጉር እነዚህ ጫካ የከረሙ ተዋጊወች ላይ ተዘናፍሎና ትከሻቸው ላይ እየተርመሰመሰ የህንድን ዊግ አስንቆ መገኘቱ አስገራሚ አይደለም? ምን ቢያደርጉት ነው? ምንም! በቃ ስለተውት ነው! ቢበዛ ቅቤ ይቀቡት ይሆናል።
የእነዚህ ተዋጊወች እጅ መስጠት ለህብረተሰቡ ያስገኛል ከተባለው "ሰላም" ይልቅ ለሴት እህቶቻችን የፀጉር እንክብካቤ ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ ነው። እህቶቸ! ፀጉራችሁን የትም በሚመረት ኬሚካል ፍዳውን ከምታበሉት ጊዜና ገንዘባችሁን ከምታቃጥሉ መፍትሄው ቀላል ነው ተውት! መተውን የመሰለ ነገር የለም፤ ተፈጥሮ እድል ሲሰጣት ራሷን ማከም ትችላለች። (ደግሞ ፀጉር ለማሳደግ ብላችሁ ጫካ እንዳትገቡ...እናተና ውበትኮ...) እዳሪ መሬት ስለሚባል ነገር ሰምታችኋል? የተጎዳ እርሻን ለተወሰነ ጊዜ ሳያርሱ ሳይዘሩ ክፍቱን መተው ማለት ነው፤ ተፈጥሮ ታክመዋለች! በቀጣይ ሲዘራበት እንደጉድ ያመርታል። ያደከማችሁን ነገር እስኪ ተውት...ለሁሉም ነገር መተውን የመሰለ ነገር የለም። ለተፈጥሮ የማሪያም መንገድ ስጧት!
@wegoch
@wegoch
@paappii
እንኳን አገር አጥበው ቀሽረው ሊያወርሱን ...
(አሌክስ አብርሃም)
በፈረንጆቹ 2011 ጃፓን ውስጥ Fukushima የተባለ አካባቢ የመሬት መንቀጥቀጥ ተከሰተ። ያውም በሬክተር ስኬል 9.0 የተመዘገበ። በሰዓታት ውስጥ 20 ሺ ህዝብ በዘግናኝ ሁኔታ አለቀ ፣6ሺ ሰው ከከፍተኛ እስከቀላል የአካል ጉዳት ደረሰበት ፣ 2500 ሰው የደረሰበት ጠፋ ፣ ግማሽ ሚሊየን ህዝብ ቤት ንብረቱን ጥሎ ተፈናቀለ። በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሚሉት የኛ አበወች ከነገሩ በላይ ዓለምን ያስደነገጠ ሌላ ዜና ተሰማ ። ለልጅ ልጅ የሚተላለፍ ጣጣ!
ይሄ ጦሰኛ አደጋ የተከሰተባት ከተማ ወጣ ብሎ የሚገኝ የኒውክሌር ማብለያ ተቋም አለ። Fukushima Daiichi nuclear power plant ይባላል። በዓለማችት ካሉ 25 የኒውክሌር ሀይል ማምረቻወች አንዱ ነው። በአደጋው ከዚህ ግዙፍ ተቋም የራዲዮ አክቲቭ ጨረር አፈትልኮ ወጣ። ራዲዮ አክቲቭ በቀጥታ ካገኘ ማንኛውንም ህይወት ያለው ፍጡር የሚገድል እንዲሁም ውሃ ይንካ ድንጋይ ሁሉንም ቁስ በመበከል ወደገዳይ ቁስነት የሚቀይር መራዢ ጨረር ነው። በአካባቢው ላይ ለአመታት በመቆየትም ይታወቃል። ከዚህም የከፋ ነው ኬሚስትሪው። ተጠቅቶ ከአደጋ መትረፍ ቢቻል እንኳን መትረፍ አይበለው። ዓለማችንን የሚያስጨንቃት የኒውክሌር መሳሪያ የሚፈራበት አንዱ ምክንያት ይሄው ነው።
አደጋው ጋፕ ሲል ከአካባቢውን ከገዳዮ ብክለት ለማፅዳት መላው ጃፓናዊ ተረባረበ። ይሄን ሁሉ መከራ ያወራኋችሁ ቀጥሎ ለምነግራችሁ የሚያስቀና ጉዳይ ነው። በእርግጥ ብክለቱን ማፅዳት፣ ጉዳቱንም መቀነስ ይቻላል ፣ ግን መጥረጊያህን አንስተህ በሞራል ዘው የምትልበት ዘመቻ አይደለም! የረቀቀ ሳይንስ ነው። በክር ላይ የመራመድ ያህል ጥንቃቄ ልምድና ዕውቀት እንዲሁም ዕድል የሚጠይቅ ነገር! በደመነፍስ ቦታው ላይ መገኘት ወዲያው ከመሞት የእድሜ ልክ ካንሰር ፣ለሌሎችም ዘግናኝ ጉዳቶች ሊዳርግ ይችላል። መቸስ ችግር ጀግኖችን ይፈጥራል። መላው ዓለም
"Fukushima 50"ብሎ የሰየማቸው ጡረታ የወጡ ሽማግሌወች ይህን ራዲዮ አክቲቭ ጉዳት ለመከላከል በፈቃደኝነት ከፊት ተሰለፉ።
እነዚህ ሰወች የጡረታ ክፍያቸው ያነሰባቸው ፣ ከዚህ ኑሮ ሞት ይሻላል ያሉ ጧሪ አልባ ሽማግሌወች እንዳይመስሏችሁ ፣ ከፍተኛ የኒውክሌር ኢንጅነሮች፣ ተመራማሪወች የነበሩ ጡረታ ወጥተው የተንደላቀቀ ኑሮ የሚኖሩ ጃፖናዊያን አባቶች እንጅ። ብቸኛ ዓላማቸው የድርሻችንን ኑረናል ይህን የኒውክሌር ተቋም የመሰረትነውም እኛ ነን ሀላፊነቱን መውሰድ ያለብን እኛ ነን፣ ልጆቻችንና ለቀጣዮ ትውልድ ይሄን ገዳይ ቆሻሻ አናወርስም! የድርሻውን ንፁህ አገር ይረከብ ዘንድ ሞትም ቢሆን ዋጋ እንክፈል የሚል ነበር። አንዷ የ72 ዓመት ጡረተኛ እንዲህ አለች "My generation built these nuclear plants. So we have to take responsibility for them. We can't dump this on the next generation,"እናም ወጣቶቹንና ብዙ ሊሰሩ የሚችሉትን ኢንጅነሮች ተክተው በዛ ቀውጢ ወቅት ወደተበከለው ተቋም ባጭር ታጥቀው ገቡ።
በእርግጥም ይህን ከባድ ሀላፊነት በመወጣት አደገኛውን ስራ በመፈፀም ከኋላ ለሚመጡ ወጣት ኢንጅነሮች እና ብክለቱን ለማፅዳት ለተሰለፉ ሁሉ መንገድ ጠረጉ። ጣቢያው ውስጥ ለቀናት በመቆየትና ሪአክተሩን በማቀዝቀዝ ጃፓን ይገጥማት ከነበረ የሚሊየኖች ሞት ታደጓት! ትውልድን ከቆሻሻና የሀዘን ታሪክ ውርስ ታደጉ!! የሚደንቀው ነገር አንድኛቸውም በአደጋው አልሞቱም!! አገር ለትውልድ እንዲህ ታጥቦ ተቀሽሮ በውርስ ይሰጣል ። እኛስ? እንኳን አገር አጥበው ቀሽረው ሊያወርሱን የኛን ዕድሜ የሚቀሙ፣ የቀጣዮ ትውልድ ዕጣፋንታ ላይ የጥላቻ ቆሻሻ ደፍተው የሚፎክሩ አባቶች ልጆች ሆንን ! አየህ ወጣትን እየማገዱ ኑሯቸውን ለሚያመቻቹ የጠነዙ ፖለቲከኞቻችን ይሄ ጅልነት ነው። ጃፓን እንደምን ሰለጠነች ይሉናል አገራችን እንደምን ሰየጠነች ብለን ስንጠይቅ!
@wegoch
@wegoch
@paappii